Fitih le Ethiopia

I wish democracy and unity for Ethiopia

Archive for the month “February, 2014”

ቦይንግ 767 – እገታ እና እንድምታው (ክንፉ አሰፋ)

abera

Hailemedhin Abera

          አንድ የኢህአዴግ ካድሬ፣  ቤት ለመከራየት ወደ አንዲት ወይዘሮ መኖርያ ይሄዳል።  ስፍራው እንደደረሰ ሌላ ተከራይም ከወይዘሮዋ ቤት ብቅ እንዳለ አስተዋለ። ሌላኛው ተከራይ ሰይጣን ነበር።  ሁለቱ ተከራዮች ሰርቪስ ቤቱን ለመያዝ እንደ ጨረታ ብጤ ጀመሩ።  ሰይጣኑ 400 ሲጠራ፣ ካድሬው ግን 500 ሊሰጥ ተስማማ።  በመጨረሻ፣ ወይዘሮዋ ቤቱን ለሰይጣኑ በትንሽ ዋጋ ማከራየቱን መረጡ። የወይዘሮዋ ውሳኔ እንግዳ ነገር ነበር።  ለሰይጣን፣ ለዚያውም በትንሽ ዋጋ ቤታቸውን ለመስጠት የወሰኑበትን ምክንያት ሲጠየቁ፤ “ሰይጣኑ አልወጣ እንኳን ቢል በጸበል ይለቃል። ካድሬው ገብቶ ቤቴን አልለቅም ቢለኝ ምን ላደርግ ነው?”  ነበር ያሉት ወይዘሮዋ። ከፍ ባለ ገንዘብ ለኢህአዴጉ ሰርቪስ ቤታቸውን ቢያከራዩት ኖሮ ባጭር ጊዜ ዋናውን ቤታቸውን ለቀው የመውጣት ክፉ እድል ይገጥማቸው ነበር።

          ዶ/ር መረራ ጉዲና ባለፈው ሳምንት ዘ ሄግ ላይ ስለ ወቅታዊ የኢትዮጵያ ሁኔታ ሲነግሩን ጣል ያደረጓት ቀልድ ናት። የዚህች ቀልድ የፖለቲካ እንድምታ ቀላል አይደለም። መልእክትዋ ሲጠቃለል የኢትዮጵያን ህዝብ እየለቀቀ መሆኑን ትነግረናለች። እየከፋ የመጣው የኑሮውና የፖለቲካ ሁኔታ የህዝቡን አእምሮ ብቻ አይደለም እየነካው ያለው። ህዝቡ እየተገፋ ሃገርሩን ለቆ እንዲሰደድ እየተገደደም ይገኛል።  በተለይ ደግሞ ሃገሪቱ በድህነት ያስተማረቻቸው ምሁሮችዋንና ባለሞያዎችዋን እንደዋዛ እያጣች ከመጣች እነሆ ሁለት አስርተ-ዓመታት ተቆጠሩ።

እለተ ሰኞ የካቲት 10፣ 2006 ዓ.ም.።

የአለም ዜና ርዕስ ሁሉ ትኩረት የጣለው በኢትዮጵያዊው ፓይለት ጉዳይ ላይ ነበር። እንደዚህ አይነት ክስተት ሲፈጸም አዲስ አይደለም። ግን ይኽኛው ልዩ ነው። ይዘቱ ለየት ይበል እንጂ  በ 1998 (እ.ኤ.አ.) ዩዋን ቢን በተባለ ቻይናዊ ፓይለት ከተፈጸመው ድርጊት ጋር ይመሳሰላል። የ30 አመቱ ወጣት የበረራ ቁጥር CA905 የሆነውን የቻይና አውሮፕላን በመያዝ የታይላንድን የአየር ጠረፍ ሰብሮ ገባ። የ27 አመት እድሜ ያላት ሚስቱን ይዞ ታይዋን ላይ ያረፈው ፓይለት ለዚያ አደገኛ ውሳኔ የሰጠው ምክንያት የኢኮኖሚ ችግር ነበር።  የደረጃ እድገት፣ የደሞዝ ጭማሪ፣ የመሳሰሉ ከራስ ወዳድነት ያላለፉ ጥያቄዎች በማንሳት የፓይለቱ የራሱን ክብር ዝቅ አደረገው።   ሙሉውን ለማንበብ እዚህ ይጫኑ…

EMF

posted by Gheremew Araghaw

 

የባህር ዳር ህዝብ ሆ ብሎ ወጣ!! ህዝቡ “ከባዶ ጭንቅላት… ባዶ እግር ይሻላል፡፡” አለ!

(ዜና ጥንቅር ዳዊት ከበደ ወየሳ)
የተቃውሞ ሰልፉ መነሻ የብአዴኑ ምክትል ሊቀመንበር አለምነው መኮንን የአማራውን ህዝብ በመናቅ እና በመሳደብ የተናገሩት ቃል ነው:: አማራውን… “በባዶ እግሩ እየሄደ ሌላውን ይንቃል” ካሉ በኋላ ለአማራው የሚቆረቆሩትን ደግሞ “ለሃጫቸውን…” እና የመሳሰሉትን እዚህ ላይ ለመጻፍ የምንጸየፋቸውን ቃላቶች ጭምር በመጠቀም አሽሙር አይሉት ስድብ ሰንዝረዋል:: ነገሩ ከአንድ የአማራን ህዝብ እወክላለሁ ወይም እመራለሁ ከሚል ሰው የሚጠበቅ ባለመሆኑ ብዙዎችን አሳዝኗል፣ አናዷልም::

በመሆኑም የአንድነት እና የመኢአድ ፓርቲዎች በጥምረት ሆነው በባህር ዳር ከተማ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ ወሰኑ:: ምክትሉ ሊቀመንበሩ ከሰልፉ በፊት እንደበፊቱ በትእቢት ተወጥረው ሳይሆን ረጋ ብለው ምን ለማለት እንደፈለጉ ቢያስረዱም ህዝቡ ግን ተቃውሞውን ቀጠለበት:: ለነገሩ በዚህ አጋጣሚ ሌሎች የሚነሱ የህዝብ ብሶቶች እንዳይነሱ በመስጋት የክልሉ አስተዳዳሪዎች አንዳንድ እንቅፋቶችን ለመፍጠር መሞከራቸው አልቀረም:: እርግጥ ነው… ተቃዋሚ ፓርቲዎቹ የተቃውሞ ሰልፉን ለማድረግ ሲዘጋጁ ብዙ እክል ገጥሟቸው ነበር:: ከተማ ውስጥ በራሪ ወረቀት መስጠት እና ቅስቀሳ ማድረግ ጭምር ተክልክለዋል:: ሆኖም ህዝቡ ራሱ ከልካዮቹን በመቃወሙ የፖሊሶቹ እገታ እና ጫና በረድ አለ:: ተቃዋሚዎቹ በባዶ እግር መሄድ ማለት ምንም ማለት እንዳልሆነ ለማሳየት ቅስቀሳ ሲያደርጉም ሆነ ዛሬ በሰላማዊ ሰልፉ ላይ… ጫማቸውን አውልቀው በባዶ እግራቸው ነበር የታዩት::

bahrdar demo13 2232014

ዛሬ እሁድ… እ.ኢ.አ የካቲት 16, 2006 ባህር ዳር ቀበሌ 12፣ ግሽ አባይ በሚገኘው የአንድነት ፓርቲ ጽ/ቤት አካባቢ ሰልፉ ሲጀመር የተለያዩ መፈክሮች እየተደመጡ ነው፡፡ በሰልፉ የፊት ረድፍ ላይ የፓርቲው ሊቀ መንበር ኢንጂነር ግዛቸው፣ ዶ/ር ኃይሉ አርአያ እና ሌሎችም አመራሮች ከህዝቡ ጋር ሆነው ታይተዋል:: ከግሽ አባይ የተነሳው ሰልፈኛ ጉዞውን በባህር ዳር ጎዳናዎች ላይ ማድረግ ሲጀምር ሌሎች በሺህ የሚቆጠሩ የከተማው ነዋሪዎች ሰልፈኛውን ተቀላቅለዋል:: የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ የያዙ ወጣቶች ከፊት ሆነው መፈክር በማሰማት ከተማዋን ከጠዋት እንቅልፏ አባነኗት:: የባህር ዳሩን የተቃውሞ ሰልፍ የአንድነት ፕሬዝዳንት ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው፣ የመኢአድ ፕሬዝዳንት አቶ አበባው መሃሪ፣ የትብብር ለዴሞክራሲ ሰብሳቢ አቶ ግርማ በቀለ እንዲሁም የአንድነት ፓርቲ ብሄራዊ ምክር ቤት አባል የሆኑት አንጋፋው ፖለቲከኛ ዶ/ር ኃይሉ አርአያ ከፊት በመምራት ላይ ይገኙ ነበር::
bahrdar demo7 2232014

ከባህር ዳር በደረሰን ዘገባ መሰረት… ህጻናት ልጆቻቸውን በጀርባቸው ያዘሉ፣ በዊልቼይር የሚሄዱ፣ አዛውንቶች፣ ወጣቶች በአንድነት ሆነው በባህርዳር ከተማ የተቃውሞ ድምጻቸውን አሰምተዋል፡፡
bahrdar demo9 2232014
ሰልፉ ከመጠናቀቁ በፊት ቁጥራቸው 15 ሺህ ያህል ሰዎች እንደነበሩ ነው ከስፍራው የተዘገበው:: በወቅቱ ከተያዙት መፈክሮች የተወሰኑት…
“የመሬት ቅርምቱ ያብቃ!”
“ህዝብን ከርስቱ ማፈናቀል ይቁም”
“ገበሬው በገዛ መሬቱ ስደተኛ አይሆንም”
“የህዝብን ክብር የደፈሩት አቶ አለምነው ለፍርድ ይቅረቡ”
“ከባዶ ጭንቅላት ባዶ እግር ይሻላል”
“ህዝብን እየሰደቡ መግዛት አይቻልም”
“ድል የህዝብ ነው”
“አቶ አለምነው የሰደቡት የአማራን ህዝብ ብቻ አይደለም”
“ብአዴን /ኢህአዴግ የአማራን ህዝብ የመምራት የሞራል ልእልና የለውም”

ከስፍራው ሁኔታውን እየተከታተለ በቀጥታ ሲዘግብ የነበረው ነብዩ ሃይሉ እንደገለጸው ከሆነ… በሰልፉ ላይ አቶ አለምነው በአማራ ህዝብ ላይ የተናገሩት የጥላቻ ንግግር ለሰልፈኛው ተለቆ ህዝቡ ንግግሩን በቁጭት በብአዴን ላይ ተቃውሞውን እያሰማ ነው፡፡
“ክብራችንን የደፈሩት የብአዴን አባላት ለፍርድ ይቅረቡ”
“ነፃነታችን በእጃችን ነው”
“ከባዶ ጭንቅላት ባዶ እግር ይሻላል፡፡”
“ብአዴን የአማራን ህዝብ ለመምራት የሞራል ልዕልና የለውም”
“መተማ የኛ ነው፣ ቋራ የኛ ነው” በሰልፉ ላይ ከተስተጋቡ መፈክሮች መሀከል ይገኝበታል፡፡ ሰልፉ በህዝብ እንደታጀበ ቀጥሏል፡፡

በመጨረሻም የየፓርቲዎቹ ተጠሪዎች ለህዝቡ ንግግር አድርገዋል:: አቶ አበባው መሃሪ 1-አቶ አለምነው መኮንን በህግ እንዲጠየቅ
2- ብአዴን የአማራ ህዝባ ወኪል ነኝ ማለቱን እንዲያቆም
3-አቶ አለምነው መኮንን የአማራን ህዝብ ይቅርታ እንዲጠይቁ አሳስበዋል፡፡
የትብብር ለዴሞክራሲ ሰብሳቢ አቶ ግርማ በቀለ በንግግራቸው… አቶ አለምነው እንዲህ እንዲናገሩ ያደረገውን አምባገነን የኢህአዴግ ስርአት ለመቀየር እንስራ ብለዋል፡፡

የሰላማዊ ሰልፉን የመዝጊያ ንግግር ያደረጉት የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ፕሬዘዳንት ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው ናቸው፡፡ ኢንጂነሩ የመግቢያ ንግግራቸውን የከፈቱት በዛሬው እለት ደስ ካሰኙን መፈክሮች “ከባዶ ጭንቅላት ባዶ እግር ይሻላል” የሚለውን በማለት ነበር፡፡ ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው በንግግራቸው መጨረሻ ላይ አቶ አለምነው ይቅርታ ካልጠየቀና በህግ ፊት ካልቀረበ አንድነት በድጋሚ በባህርዳር የተቃውሞ ሰልፍ እንደሚጠራ አሳውቀዋል፡፡

አሁን ሰልፉ ተጠናቆ ህዝቡ በሰላም እንደወጣ፣ በሰላም ወደ ቤቱ እየተመለሰ ነው:: የሰላማዊ ሰልፉ በሰላም መጠናቀቅ የህዝቡን ጨዋነትና የአመራሩን ብስለት ያሳያል:: እርግጥ ነው… ሰላማዊ ሰልፉ ተጠናቆ ህዝቡ በሰላም ወደቤቱ ቢያመራም… ባህር ዳር ላይ የተለኮሰው የመነቃቃት ስሜት ግን በቀላሉ የሚበርድ አይመስልም:: እኛም መልካሙን ሁሉ እየተመኘን ዘገባችንን እዚህ ላይ አጠናቀናል::

EMF

posted by Gheremew Araghaw

የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ “የረዳት አብራሪው አኩሪ ገድል የኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃ እስኪወጣ ይቀጥላል” አለ

 

“የወጣት ሃይለመድህን አበራ አኩሪ ገድል የኢትዮጵያ ህዝብ ነፃነትእውን እስኪሆን ድረስ ይቀጥላል” ሲል የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ ባወጣው መግለጫ አስታወቀ። ንቅናቄው ለዘ-ሐበሻ በላከው መግለጫው ረዳት አብራሪ ሃይለመድህን አበራ ለአለም ህብረተሰብ ያስተጋባው መልዕክት የሁሉም ኢትዮጵያዊ ድምፅን ነውና፤ አላማና ተግባሩም የሁሉም ኢትዮጵያዊ ምኞትና ፍላጎት መሆኑን በፅኑ ያምናል” ብሏል። በተጫምሪም አኩሪ ተግባር ፈጽሟል ላለው ለረዳት አብራሪው የንቅናቄው የክብር አባል እንዲሆን የምስክር ወረቀት ሰጥቷል፡፡ ሙሉ መግለጫው ከምስክር ወረቀቱ በታች እንደወረደ እንደሚከተለው ተስተናግዷል።

 

“የወያኔ/ኢህአዴግ ጨቋኝ ሥርዓት በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ቁጥር ስፍር የሌላቸው አፋኝ ህጎችን በመጫን፤ እንዳሻው ንጹሃን ዜጎችን መጥፎ ስም በመስጠት፤ ባልሰሩት ሃጥያትና በተፈበረከ የሃሰት ወያኔያዊ ውንጀላ በየእስር ቤቱ እንዲማቅቁ እያደረገ መሆኑ ለማንኛውም ኢትዮጵያዊ ግልጽ ነው። ይህ አፋኝ ሥርዓት የምንወዳት ሃገራችን ኢትዮጵያንና ህዝቧን የማጥፋት እኩይ አላማ ሰንቆ፤ ምሁራን ዜጎች ለሚወዷት ሃገራቸውና ለሚሳሱለት ህዝባቸው የበኩላቸውን ማበርከት እንዳይችሉ፤ በተለይ ወጣት ምሁራን በሃገራቸው ጉዳይ ላይ ቀጥተኛ ተሳተፊ እንዳይሆኑ ከፍተኛ ግድያ፣ እንግልት፣ ጭቆና፣ በደልና፣ ወከባ እያደረገ ይገኛል።

ይህ ፋሽስት ሥርዓት በዘረጋው አፋኝ መዋቅር ህዝብ እርስ በርሱ በጥርጣሬ እንዲኖር፤ ቤተሰብ ከቤተሰብ እንዳይተማመን፤ አንዱ ብሄር በሌላው ብሄር ላይ ጥላቻ እንዲኖረውና፤ አንዱ ሃይማኖት ከሌላው ሃይማኖት ጋር በፍቅር፣ በመተሳሰብና፣ በመቻቻል እንዳይኖር፤ ባጠቃላይ በሃገሪቷ ሰላምና መረጋጋት እንዳይኖር፤ ብሎም ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ከምድረገጽ ፈፅሞ ለማጥፋት፤ ያልፈነቀለው ድንጋይ ባይኖርም፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ያስተሳሰረው የፍቅርና አብሮ የመኖር አኩሪ ባህሉ ነውና፤ የወያኔ/ኢህአዴግ እልቆ መሳፍርት መሰሪ ተንኮልና ደባ ሳያንበረክከው፤ ሥርዓቱ በወጠነው መንገድ ሳይሆን በፍቅር፣ በመተሳሰብና፣ በመቻቻል አንድነቱን ጠብቆ አሁን ድረስ መዝለቅ ችሏል።

የታፈነ ጭስ መውጫ አያጣም ነውና፤ ታጋሽና ሰላም ወዳድ የሆነው የኢትዮጵያ ህዝብ ጭቆናውና በደሉ ከልክ በላይ ስለሆነበት፤ እየደረሰበት የሚገኘውን ቅጥ ያጣ ግፍ በተለያዩ አያሌ መንገዶች ሲገልጽ ቆይቷል። በየካቲት 10, 2006 የኢትዮጵያ አየር መንገድ አብራሪ በሆነው ወጣት ሃይለመድህን አበራ የተፈጸመው አኩሪ ተግባር ይህንኑ የስርዓቱን አስከፊ ገጽታና በህዝብ ላይ የሚደርሰዉን ግፍ፣ ወከባ፣ እንግልት፣ እስራት፣ ግድያና፣ ሰቆቃ የሚያረጋግጥ አይነተኛ ክስተት ነው። ወጣት ሃይለመድህን አበራ በሥርዓቱ እየደረሰበት የነበረዉን አስከፊ በደል ለማምለጥ በግሉ በርካታ መንገዶች ነበሩት። የአውሮፕላን አብራሪ በመሆኑ አለም ላይ ካሉ ሃገራት ሁሉ በሚፈልግበት የመሄድና የመኖር እድሉ በእጁ ነበር። በኢኮኖሚም ቢሆን በሃገሪቱ ከፍተኛ ክፍያ ከሚያገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች አንዱ በመሆኑ በግል ኑሮው ተንደላቆ የመኖር ችሎታው እንደነበረው ለማንም አጠራጣሪ አይሆንም።

ነገር ግን ወጣት ሃይለመድህን አበራ የኢትዮጵያ ህዝብ ቁስል ስላመመው፤ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የሚደርሰው ግፍና በደል የሱም እንደሆነ ቀድሞ ስለተረዳ፤ ህልሙ የኢትዮጵያ ህዝብ ነፃነት እውን ሆኖ፤ መብቱ ተከብሮለት፤ በሃገሩ የመኖር ተስፋን አንግቦ፤ በፍቅር፣ በሰላምና፣ በኢትዮጵያዊነት መንፈስ ሲኖር ማየት በመሆኑ፤ በዙሪያው የጨበጠው እድል ሳያጓጓውና ወጣትነት ሳያታልለው፤ በማስተዋል ለኢትዮጵያ ህዝብ ነፃነት እጅግ ከፍተኛ መሥዕዋትነትንና ጀግንነትን በተግባር ፈጽሟል።

የወጣት ሃይለመድህን አበራ ታላቅ ተግባር የወያኔ/ኢህአዴግ ከልክ ያለፈ ግፍንና የኢትዮጵያ ህዝብን የታፈነ ሰቆቃ ለአለም ህዝብ በይፋ ከማጋለጡም ባለፈ፤ በኢትዮጲያችን እጅግ ብዙ እሱን መሰል ጀግና ወጣቶች ያለጥርጥር እንደሚገኙና፤ በኢትዮጵያ ነፃነት፣ ፍትህና፣ እኩልነት በአስተማማኝ ሁኔታ እውን እስኪሆን ድረስ፤ ህዝብ ለነፃነቱ ምንግዜም እንደማይተኛ ያረጋገጠ ብሄራዊ የጀግንነት ተግባር ነው። በመሆኑም ወጣት ሃይለመድህን አበራ ለኢትዮጵያ ህዝብ ነፃነት የፈፀመው አኩሪ ተግባርና የከፈለው ታላቅ መሥዕዋትነት በኢትዮጵያ ህዝብ ዘንድ ለዘላለም ሲታወስ እንደሚኖር ጥርጥር የለንም። ነገር ግን በዚህ ውድ ኢትዮጵያዊ ጀግና የተከፈለው ታላቅ መሥዕዋትነት በኢትዮጵያ ሰላም፣ ፍትህ፣ እኩልነትና፣ ተስፋ እንዲመጣ በቁርጠኝነት የታቀደ በመሆኑ፤ ውጥኑ ለታለመለት አላማ ግቡን እንዲመታ፤ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ እድሜ፣ ሃይማኖት፣ ብሄር፣ ወይንም ሌላ ማንኛውም ልዩነቱ ሳይገድበው፤ ለጋራ ነፃነቱ በጋራ በመነሳት አንድነቱን ለአለም ማሳየትና የዚህን ቆራጥ ኢትዮጵያዊ ጀግንነት ማስተጋባት ይኖርበታል።

የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ ወጣት ሃይለመድህን አበራ ለአለም ህብረተሰብ ያስተጋባው መልዕክት የሁሉም ኢትዮጵያዊ ድምፅን ነውና፤ አላማና ተግባሩም የሁሉም ኢትዮጵያዊ ምኞትና ፍላጎት መሆኑን በፅኑ ያምናል። ስለሆነም ንቅናቄያችን በአለም ዙሪያ የሚገኙ አባላቶቹን ሙሉ በሙሉ በማስተባበር፤ የወጣት ሃይለመድህን አበራን ድምፅ መልሶ በማስተጋባት፤ አንድነቱን ለአለማቀፉ ህብረተሰብና ለአለም መንግስታት፣ እንዲሁም ለሚመለከታቸው አለማቀፋዊ ተቋማት በሙሉ በማስመስከር፤ እውነታዉን ለማሳወቅ የተለያዩ ሰላማዊ ሰልፎችን፣ ዲፕሎማሲያዊ ሂደቶችንና፣ ሌሎች ተዛማጅ ተግባራትን በማከናወን፤ ግንባር ቀደም ሚና እንደሚጫወት ከወዲሁ እያስታወቀ፤ ወጣት ሃይለመድህን አበራ ለኢትዮጵያውያን የነፃነት ትግል ላበረከተው ታላቅ አስተዋዕፅዎ ብሄራዊ ጀግና ሲል መሰየሙን ለኢትዮጵያ ህዝብ በታላቅ ኩራት እያበሰረ፤ የብሄራዊ ጀግና የክብር የምስክር ወረቀት በአድናቆት ያበረክታል።

የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ በዚህ ዘረኛ የወያኔ/ኢህአዴግ መንግስት ከልክ ያለፈ ጭቆና፣ ረገጣና፣ እንግልት ሠለባ ሆኖ በመሰቃየት ላይ ለሚገኘው የኢትዮጵያ ህዝብ ተቆርቋሪ ለሆናችሁና በምንወዳት ሃገራችን ሰላም፣ ነፃነት፣ ፍትህ፣ ተስፋ እንዲሰፍንና ለህዝብ የሚበጅ ቀና ለውጥ ለዘለቄታው ይሰፍን ዘንድ ለምትመኙ ሃገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን በሙሉ፤ እንዲሁም ለተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ ለሃይማኖት ተቋማትና፣ ለሲቪክ ማህበራት ታላቅ ሃገራዊ ሃላፊነትና የህዝብ አደራ በጫንቃችሁ እንደተሸከማችሁ በመገንዘብ፤ ልዩነታችሁን ወደ ጎን በመተው ለዚህ ወሳኝ ህዝባዊ ጥሪ በአንድነት ምላሽ በመስጠት የሚጠበቅባችሁን ህዝባዊ አደራ እንድትወጡ ዘንድ በጥብቅ እያሳሰበ፤ ሃገራዊ የመተባበር ጥሪውን በአክብሮት ያቀርባል።

የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ

Ze-Habesha 

 
posted by Tseday Getachew

ኢትዮጵያውያን ረዳት ፓይለቱን በመደገፍ በዋሽንግተን ዲሲ የስዊዘርላንድ ኢምባሲ ደጃፍ የፊታችን ሰኞ ሰልፍ ሊወጡ ነው

(ዘ-ሐበሻ) ሰኞ ዕለት ሮም ላይ ማረፍ የነበረበትን አውሮፕላን ስዊዘርላንድ ላይ እንዲያርፍ ያደረገው ኢትዮጵያዊው ረዳት ፓይለት “የታፈነውን የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ጥሰት ለዓለም ያሳየ ጀግና ነው” የሚሉ ኢትዮጵያውያን የፊታችን ሰኞ ጠዋት ፌብሩዋሪ 24 ቀን 2014 ዓ.ም በዋሽንግተን ዲሲ የስዊዘርላንድ ኢምባሲ ደጃፍ ላይ ሰላማዊ ሰልፍ ጠሩ። የስዊዘርላንድ መንግስት ነገ ወይም ከነገ በስቲያ በረዳት አብራሪው ሃይለመድህን አበራ ዙሪያ ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ አስታውቋል።

በዋሽንግተን ዲሲ የስዊዘርላንድ ኢምባሲ ደጃፍ የተጣራው ይኸው ሰልፍ ረዳት አብራሪው አውሮፕላን ጠላፊ አሸባሪ እንዳልሆነና ድርጊቱን የፈጸመው በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገውን የሰብአዊ መብት ጥሰት፣ በስርዓቱ ውስጥ የሰፈነውን የአንድ ብሔር የበላይነትን ለዓለም ለማሳየት የተጠቀመበት ዘዴ በመሆኑ የስዊዘርላንድ መንግስት የጥገኝነት ጥያቄውን እንዲቀበለው እንደሚጠይቅ ከሰልፉ አስተባበሪዎች ለዘ-ሐበሻ የደረሰው መረጃ ያመለክታል።

“ለወገን ደራሽ ወገን ነውና ይህ ወንድማችን ለኛ ነፃነት የታፈነውን ያገራችንን ህዝብ በአለም አደባባይ ያንድ ዘር ብቻ የነገሰው የዘረኛው ወያኔን ስራ ለአለም ያጋለጠ ጀግና ወንድማችን አሸባሪ ሳይሆን የነፃነት ታጋይ ወንድማችን መሆኖን ለመግለጽ ይህን ሰላማዊ ሰልፍ ተጠርቷል” ያለው የዋሽንግተን ዲሲው ሰልፍ አስተባባሪዎች ጥሪ ፍላየር ለዘ-ሐበሻ ደርሷታል። ሰልፉ የሚደረገው Embassy of Switzerland in the United States of America ሲሆን አድራሻውም ፦ 2900 Cathedral Ave., NW, Washington, D.C. ነው።

ረዳት ፓይለቱን በመደገፍ ተመሳሳይ ሰልፍ በስዊዘርላንድና በሌሎች ሃገራት ለማድረግ በዝግጅት ላይ መሆኑ የደረሱን መረጃዎች ያመለክታሉ።

ይህ በ እንዲህ እንዳለ የስዊዘርላንድ መንግስት በረዳት አብራሪው ሃይለመድህን አበራ ዙሪያ ነገ ወይም ከነገ በስቲያ ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ አስታውቋል። ይህንን ተከትሎም በርካቶች ጋዜጣዊ መግለጫውን በጉጉት በመጠባበቅ ላይ ያሉበት ሁኔታ ነው ያለው።

Ze-Habesha

posted by Tseday Getachew

ሰበር ዜና፤ ወያኔ በውጭ የሚገኙ ተቃዋሚዎችና ጋዜጠኞች ላይ የሚያደርገው የስለላ ወንጀል ስለተጋለጠ አሜሪካ ውስጥ ክስ ተመሠረተበት

ሰበር ዜና

ወያኔ በውጭ በሚገኙ ተቃዋሚዎችና ጋዜጠኞች ላይ በሚያደርገው የስለላ ወንጀል ስለተጋለጠ አሜሪካ ውስጥ ክስ ተመሠረተበት

ዜናውን በፒ.ዲ.ኤፍ. ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ።  ወያኔ በስለላ ወንጀል አሜሪካ ውስጥ ተከሰሰ

የኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ለ22 ዓመታት የግድያ፣ የማሰቃየት፣ የማፈንና ሌሎችም ዘግናኝ ወንጀሎችን ሲፈጽም የኖረው ወያኔ “ተሸሽጎ የሚኖር ነገር የለም” እንደሚባለው አሜሪካ ውስጥ በሚገኘው የኢሳት ጋዜጠኞች ላይ ያካሂድ የነበረው የስለላ መረብ በመበጣጠሱና እጅ ከፍንጅ በመያዙ በዛሬው ዕለት ዋሽንግተን ከተማ ውስጥ በሚገኘው ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውስጥ ክስ እንደተመሠረተበት ታላቁ የዋሽንግተን ፖስት ጋዜጣ አስታውቋል።

ክሱን የመሠረተው አሜሪካ ውስጥ ላለፉት 22 ዓመታት የኖረው ኢትዮጵያዊ አሜሪካዊ ግለሰብ ሲሆን የወያኔ አገዛዝ የአሜሪካን ህግ በመጣስ የስለላ መረቦችን በግልኮምፒውሩ ላይ በማስጠመድ ግለሰቡ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ሲከታተል እንደነበር ተመልክቷል። ይህ የተመሠረተው ክስ የቅርብ የአሜሪካን መንግስት ወዳጅና ተመጽዋች የሆነው የወያኔ አገዛዝ ተቃዋሚዎችን፣ጋዜጠኞችንና የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎችን፣ የማፈን ታሪክ ያለው ከመሆኑም በላይ የተራቀቁ የድረገጽ መሳሪያዎችን በመጠቀም ጠላቶቼ የሚላቸውን ሲሰልል መገኘቱን ምልክት የሚሰጥ መሆኑ በጋዜጣው ውስጥ ተጠቁሟል።

ክሱን ያቀረበው “Electronic Frontier Foundation” በመባል የሚጠራው የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ድርጅት ጠበቃ የሆኑት ሚ/ር ኔት ካርዶዞ እንደገለጹት “የኢትዮጵያ መንግሥት የሚቻለውን ሁሉ በማድረግ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን በተለይም ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ግንኙነት አላቸው የሚላቸውን እንደሚሰልል መረጋገጡን አስታውቀዋል። የወያኔ ወኪሎች ስለቀረበባቸው ክስ ማብራሪያ እንዲሰጡ ተጠይቀው የሰጡት መልስ የተለመደ ክህደታቸውንና ቅጥፈታቸውን ነው። የኮምፒውተር ተመራማሪዎች እንዳረጋገጡት የወያኔ አገዛዝ የአፈናና የስለላ ወንጀሎችን ከሚፈጽሙ አገሮች ተርታ ውስጥ ይገኛል።

ከአራት ወራት በፊት ነጻ የሆነው የጥናትና ምርምር ተቋም የወያኔ አገዛዝ “ፊን እስፓይ” በመባል የሚጠራ የጆሮጠቢ መረብ እንደሚጠቀም መረጃዎች መገኘታቸውን የሚያሳይ ዝርዝር ዘገባ አቅርበው ነበር። ቶሮንቶ ዩኒቨርስቲ ውስጥ በሚገኝው ዓለም-አቀፍ ጉዳዮች ትምህርት ቤት የወያኔ አገዛዝ የስለላውን መረብ ብቸኛ ተጠቃሚ መሆኑን አርጋግጠዋል። ይህ ሪፖርት ከወጣና ዜናው ከፍተኛ ሽፋን ከተሰጠው ከ5 ቀናቶች በኋላ የወያኔ አገዛዝ መጋለጡን በማወቅ ያካሂድ የነበረውን የስለላ መረብ ማቋረጡ ታውቋል። ሆኖም የወያኔ የስለላ  መረብ ባላሟሎች እንዳይያዙ መረጃዎችን ለማጥፋት ከፍተኛ ርብርቦሽ ቢያደርጉም ሙሉ በሙሉ አሻራቸውን ለማጥፋት ሳይችሉ በመቅረታቸው እጅ ከፍንጅ ሊያሲዝቸው የሚችል መረጃ ተገኝቶባቸዋል።

ከዚህም በተጨማሪ ወያኔ እንግሊዝ አገር ውስጥም በሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን የፖለቲካ ስደተኞች ላይ የሚያደርገው ስለላ ስለተደረሰበት ተጨማሪም ክስ ተመስርቶበታል። ከዚህ ለማጠቃለል የሚቻለው ወያኔ የአሜሪካን ህግ በመጣስ አማሪካ መሬት ላይ የፈጸመው ወንጀል ከአሜሪካ መንግስት ጋር ያለውን ግንኙነት በእጅጉ እንደሚያበላሽበት አይጠረጠርም። የዚህ ወንጀል መፈጸም መጋለጥና ክስ መመስረት ለወያኔ አገዛዝ ድጋፍ የሚሰጡ የአሜሪካን ባለሥልጣኖችንም ጭምር በወያኔ ድፍረትና ጥጋብ በአገራቸው ምድር ላይ ወንጀል መፈጸሙ በእጅጉ እንደሚያበሳጫቸውና እንደሚያስቆጫቸው እንዲሁም “ያሳደኩት ውሻ ነከሰኝ” እንደሚያስብላቸው ይገመታል። በአጠቃላይ ወያኔ ይህንን የስለላ ወንጀል ሲፈጽም እጅ ከፍንጅ መያዙ እንደ መንግስት ሳይሆን ወንበዴነቱን፣ሌብነቱን፣ማጅራት መቺነቱንና ኪስ አውላቂነቱን በዓለም-አቀፍ ደረጃ ያሳየና እርቃኑን ያስቀረው መሆኑን ለመገመት አያዳግትም። ከዚህም በተጨማሪ ወያኔ ከደደቢት ዋሻ ውንብድናውን ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስከ አሁን ድረስ በርካታ ደረቅ ወንጀሎችን ለምሳሌም ባንኮችን፣ ትምህርት ቤቶችን፣ የመንግስት መስሪያ ቤቶችን፣ ቤተክርስቲያኖችን፣ የግለሰቦችን መኖሪያ ቤቶችን፣ ሱቆችንና ሌሎች የኢትዮጵያውያንን ንብረቶችን መዝረፍ፣ ሀኪም ቤት የተኙ በሽተኞችን ከአልጋቸው አውርዶ መሬት ላይ በመጣል አልጋቸውን መዝረፍ፤ ሌሎችንም ወንጀሎች ሲፈጽም መኖሩና ብሔራዊ ባንክ የተቀመጠውን ወርቅ በምትሃት ወደ ቦንዳነት የለወጠ መሆኑና በርካታ ኩንታል ቡና ወደ አቧራነት የቀየረ መሆኑ አይዘነጋም።

EthiopianReview.com

posted by Tseday Getachew

 

ጉራማይሌ ፖለቲካ ክፍል 2 (ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ )

Journalist Temasegan Dasaleg

ባለፈው ሳምንት በተቃርኖ የተሞላ ጉራማይሌ ፖለቲካችንን በማስረጃ አስደግፎ ማየቱን ጀምረን፣ ቀሪውን በይደር ማቆየታችን ይታወሳልና እንዲህ እንቀጥላለን…
…የጎንደር ፕሮግራሜን ከጨረስኩ በኋላ ለስድስት ቀናት ያህል በባሕር ዳር ከተማ አሳልፌ ነበር፡፡ በዚህ ወቅትም ያገጠመኝን ለፖለቲካዊ ፈገግታ የሚሆን ጉራማይሌ ክስተትን በአዲስ መስመር ላካፍላችሁ፡፡

እንደሚታወቀው ጥር 17 እና 18 የአፍሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ዓመታዊ መደበኛ ስበሰባቸውን በባሕር ዳር ከተማ አድርገዋል፡፡ አብዛኞቹ ሚኒስትሮችም በከተማዋ የተገኙት በዋዜማው (ጥር 16) ነበር፡፡ ይህንንም ተከትሎ በየመቶ ሜትሩ ባለው ፍተሻ እና ‹በዚህ ማለፍ አይቻልም› በሚል እስከ አፍንጫቸው በታጠቁ ወታደሮች ክልከላ የተነሳ ከቦታ ቦታ መዘዋወሩ በቀላሉ የሚሳካ አይደለም፡፡

በአናቱም ከአዲስ አበባም ሆነ ከጎንደር ወደ ባሕር ዳር የሚገባ ማንኛውም ሰው፣ ተደጋጋሚና ጠበቅ ያለ ትዕግስት አስጨራሽ ፍተሻን ማለፍ ግዴታው ነበር፡፡ በተወሰነ የሰዓታት ልዩነትም መላ ከተማዋንና ዙሪያዋን በሚያጓራ ድምፁ እያናወፀ፣ በአየር እየተሸከረከረ የሚቃኝ የጦር ጄት ተመልክቻለሁ፡፡ በግምትም በየአስር ሜትር ዕርቀት ላይ የፌደራልና የክልሉ ፖሊሶች ለጥበቃ ከመመደባቸውም አልፎ ጣታቸውን ቃታ ላይ አሳርፈው ሲታዩ፣ ከተማዋ ከሰዓታት በፊት ከባዕድ ወራሪ ጦር ነፃ የወጣች እንጂ፣ አፍሪካውያን ባለሥልጣናት የሚሰበሰቡባት በመሆኗ ካልታሰበ አደጋ ለመከላከል የተደረገ ጥበቃ ነው ብሎ ለማመን ይቸግራል፡፡

በርግጥ ይህ ሁሉ የቅድመ-ጥንቃቄ ሽር-ጉድ ሀገሪቱ አልሸባብን ከመሰለ ልምድና አቅም ያለው የሽብርተኛ ቡድን ጋር ከገባችበት ግጭት አኳያ ብዙም የተጋነነ ላይሆን ይችላል፡፡ የጉዳዩ ግርምቢጥነትም (ጉራማይሌነትም) ይህ አይደለም፤ ከምሽቱ ገጠመኜ ጋር የተያያዘ እንጂ፡፡ ይኸውም ይህ ሁሉ የፀጥታ ጥበቃ የተደረገላቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ቴዎድሮስ አድሀኖም እና ሚኒስትር ዴኤታው ብርሃነ ክርስቶስን ጨምሮ በርካታ ባለሥልጣናት፣ ባለቤትነቱ የታዋቂዋ አርቲስት አምሳለ ምትኬ በሆነው የጭፈራ ቤት በመክተም፤ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነው አሸሼ ገዳሜአቸውን እያቀለጡ ውድቅት ሌሊቱ እስኪጋመስ ድረስ ማሳለፋቸው ነው፡፡

በዚህ ጊዜም በከተማዋ ቅጥር ከባድ ፍርሃት ያነገሰው ያ ሁሉ የጥበቃ ጋጋታ አልነበረም፤ እንዲያ በአይናቸው ብቻ አፈር ከድሜ የሚደባልቁት የደህንነት ሰራተኞችም የሉም፤ ‹ወዴት ነህ? ቁም! ተቀመጥ!› የሚልም የለም፡፡ እየተመለከትኩት ያለሁት ትዕይንት፣ በተንጣለለው ግዙፍ አዳራሽ አርቲስቷ በተስረቅራቂ ድምጿ የጥላሁን ገሰሰን ዜማ ‹‹አንቺ ከቶ ግዴለሽም፣ ስለፍቅር አይገባሽም…››ን ስታቀነቅን፣ ክቡራን ሚኒስትሮችም ጉሮሯቸው እስኪዘጋ፣ ትከሻቸውን እያርገፈገፉ ‹‹አንቺ ከቶ…››ን ተቀብለው የሚያዳምቁበትን ፈንጠዝያ ብቻ ነው፡፡

በነገራችን ላይ ይህ ጉዳይ (ከሚኒስትሮቹ የግል ነፃነት አኳያ) እንደማይመለከተኝ አውቃለሁ፤ በትርፍ ሰዓታቸውም እንዳሻቸው የመሆን መብት እንዳላቸው አምናለሁ፡፡ ግና ጉዳዩን እዚህ ጋ ለማንሳት የተገደድኩበት ገፊ-ምክንያት ያንን ሁሉ የሀገር ሀብት በማፍሰስ በተዋጊ ጄት እገዛ ጭምር ደህንነታቸው ሲጠበቅ ከማዋሉ ጋር ስለሚያያዝ ብቻ ነው፤ እንዲህ ከአፍ እስከገደፉ በታዳሚ በተጨናነቀ ጭፈራ ቤት ዘና ብለው ለማሳለፍ የሚያስችል የተረጋጋ ፀጥታ ካለ፣ ስለምንድር ነው ያ ሁሉ ጥበቃና የዜጎችን ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት መገደብ ያስፈለገው? እዚህም እዚያም ተሯሩጠው የዕለት ጉርሳቸውን የሚያሟሉ ለፍቶ አዳሪዎችንስ ሰርተው እንዳይበሉ መከልከሉ ምን የሚሉት አስተዳደራዊ ዘይቤ ነው? (በርግጥ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ የሚሰጥ እንዳሌለ አውቃለሁ፤ ምክንያቱም ‹‹ነፃ አውጪ››ው ኢህአዴግ፣ ሀገሬን ‹17 ዓመት ታግዬባታለሁና፣ ሃምሳ ዓመት እንዳሻኝ የመፈንጨት መብት አለኝ› የሚልባት መቀለጃው ካደረገ አመታት ተቆጥረዋል፡፡ እናም እንዲህ አይነቱን የጉራማይሌ ፖለቲካ ገፅታ መመልከቱ ያልተጠበቀ ሊሆን አይችልም)

ባለሐብት ወይስ ሰላይ?

በባህር ዳር ውስጥ ስሙ ተደጋግሞ ወደ ጆሮዬ የደረሰ የጎረቤት ሀገር ሰው፣ ሌላው የጉራማይሌ ፖለቲካው ማሳያ ነው፡፡ ይህ አሽራፍ የተባለ ሱዳናዊ ባለሃብት፣ በከተማዋ መረቡን ከዘረጋ አስር ዓመት እንዳለፈው ይነገራል፤ ‹‹እሰማራባቸዋለሁ›› ብሎ የነበረው የኢንቨስትመንት ዘርፎችም፡- ከመንግስት የገዛው የምግብ ዘይት ፋብሪካውን ጨምሮ ራሱ ባስገነባቸው የስጋ፣ የዶሮ፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ማቀነባበሪያ፣ የወተት ተዋፆኦ፣ ፍሌበር ወተር እና ከሱዳን የሚመጣ ጋዝ ማሸግን የሚያካትት ነበር፡፡ እንዲሁም በቡሬ-ወለጋ መንገድ አካባቢ የግራናይት እምነበረድ ማምረቻ እከፍታለሁ ብሎ መሬት ወስዷል፡፡ ይሁንና ዛሬም ድረስ የሚጠቀስ የጀመረው ሥራ እንደሌለ ሰምቻለሁ፡፡

በግቢው ውስጥ ጥቂት ሰራተኞች ውር ውር ከማለታቸው በቀር በተደጋጋሚ የሚታየው ክስተትም፣ አንድ በየሳምንቱ ሙሉውን ሰው የጫነ አውቶብስ ከካርቱም ባህር ዳር የመመላለሱ ምስጢር ነው፤ አውቶብሱ ምንጊዜም አዳዲስ ሰዎችን ይዞ ይመጣል፣ ለሳምንት ያህል የከረሙትን ደግሞ አሳፍሮ ይመለሳል፤ ይህ ሂደት ሳይቋረጥ ዛሬም ድረስ ሲደጋገም ተስተውሏል፡፡

የሚመጡት እንግዶችም አልፎ አልፎ ጀንበር ስትጠልቅ የምሽት ክለቦችንና በዚያ የሚገኙ እህቶቻችንን ሲያሳድዱ ከመመልከት በቀር፣ ለምን ስራ ወደ ባህር ዳር እንደሚመጡ እንኳንስ የአካባቢው ነዋሪ ቀርቶ፣ የክልሉ አስተዳዳሪዎችም ቢሆኑ ያወቁት አይመስለኝም፡፡ ጉዳዩን በቅርብ ከተከታተሉ የመረጃ ምንጬ እንደተረዳሁት ከሆነ ደግሞ፣ ሰዎቹ በስለላ ስራ ላይ የተሰማሩ ሳይሆኑ እንደማይቀር ነው፡፡

በመካከለኛው ምስራቅ እና ዩክሬን ጭምር ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ እንዳፈሰሰ የሚነገርለት ባለሐብቱ አሽራፍ፣ ከኢህአዴግ ጋር ከትጥቅ ትግሉ ዘመን የጀመረ ወዳጅነት እንዳለው ቢታወቅም፣ ኩነቱ ጉራማይሌ የሚሆንብን ግን የዜግነት ጉዳይን ስናነሳ ነው፤ ምክንያቱም በውሃ ቀጠነ ሰበብ ኢትዮጵያውያን ባለሀብቶችን የሚያስጨንቀው ስርዓት፣ ለሱዳናዊው ከበርቴ ወደርየለሽ ትዕግስት ከማሳየቱም በላይ ገበናውን አሳልፎ መስጠቱን መታዘብ ይቻላልና ነው፡፡ በነገራችን ላይ ከአባይ ውሃ ጋር በተያያዘም ሆነ ‹ወደ ሱዳን ሊካለሉ ነው› የሚባሉ መሬቶችን በተመለከተ የካርቱም መንግስት ወኪል እንደሆነ መረጃ አለን የሚሉ ሰዎችም አጋጥመውኛል፡፡

መቼም በታሪካችን የኢህአዴግን ያህል በብሔራዊ ስሜትና በሀገራዊ ጥቅም ደንታ ቢስ የሆነ ስርዓት ታይቶ አይታወቅም፡፡ ዳሩ ቀድሞውንስ እንዲህ ተዋርዶ ሕዝብን ከሚያሳንስ ስብስብ ምን የተሻለ ነገር መጠበቅ ይገባል?

በብአዴን ማን ይወክላል?

በዘመነ ኢህአዴግ ከታሪክ ተጠያቂነት በፍፁም ሊያመልጡ ከማይችሉ የፖለቲካ ድርጅቶች መካከል ብአዴን እና ኦህዴድ በግንባር ቀደምትነት ይሰለፋሉ፡፡ ሁለቱም ‹እንወክለዋለን› በሚሉት ሕዝብ ላይ ተደጋጋሚ ክህደት ለመፈፀማቸው፣ ደርዘን ያለፉ ድርሳናትን ማዘጋጀት እንደሚቻል እናውቃለን፡፡ አልፎ ተርፎም ህወሓትን ከመሰለ የማፍያ ቡድን ጋር ግንባር ፈጥረው ‹‹ወከልነው›› የሚሉትን የማህብረሰብ ክፍል ህልውና ማድቀቃቸው እውነት ነው፡፡ በርግጥ ምንም እንኳ የሀገር አንድነትን አደጋ ላይ የጣለ ከፋፋይ ፖለቲካን ጨምሮ ሕዝብ እና ትውልድ የሚሉ ነገሮችን ቅርጫት ውስጥ የመጣል አባዜ ቢጠናወተውም፣ ህወሓት ከቅጥረኞቹ ይልቅ የራሱ የሆነ የፖለቲካ ቁመና እና መሬት የወረደ አጀንዳ ይዞ የተነሳ መሆኑ የማይካድ እውነታ ነው፡፡

በዚህ ቁጣ እንድናገር ያደረገኝ ሰሞነኛ ምክንያት ከአንድ የብአዴን ከፍተኛ ካድሬ ነውረኛነት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ይህ ሰው የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አለምነው መኮንን ሲሆን፣ ኢህአዴግን የተቀላቀለው በተወለደበት ሰሜን ወሎ በ1982 ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ ነበር፡፡ ከመንግስት ለውጥ በኋላም ረዝም ላለ ጊዜ በዛው በሰሜን ወሎ ከገዱ አንዳርጋቸው ጋር በኢህዴን /ብአዴን/ ተጠሪነት ሰርቷል፤ ከሲቪል ሰርቪስ ኮሌጅ የመጀመሪያ ዲግሪውን ማግኘቱን ተከትሎም በክልሉ አስተዳደር ስር ባለው በምፃረ ቃል ‹‹SRAR›› ተብሎ በሚጠራው (በእርሻና መልሶ ማቋቋም ላይ በሚያተኩር) ተቋም በአንድ ክፍል ኃላፊነት አገልግሏል፡፡ በምርጫ 97 ዋዜማ ደግሞ የክልሉ የማስታወቂያ ቢሮ ኃላፊ እንደነበር ይታወሳል፤ ቀጥሎም የአማራ ዲዛይንና ቁጥጥር ስራ አስኪያጅ ሆኖ ሰርቷል፤ ከ2004 ዓ.ም
መጨረሻ ጀምሮ ደግሞ የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት እና የብአዴን ቢሮ ኃላፊ ነው (በነገራችን ላይ በአማራ ክልል ምክትል ፕሬዚዳንቶች ሶስት ናቸው፤ ከአለምነው በተጨማሪ ብናልፍ አንዱአለም እና ዶ/ር አምባቸው የተባሉ ተሿሚዎችም አሉ) የሆነው ሆኖ ይህ ሰው ባለፈው ሳምንት በባህር ዳር በተዘጋጀ አንድ ስብሰባ ላይ የተናገረውን አስነዋሪ ነገር፣ ረዥም ዕድሜ ለኢሳት ይሁንና ጭው ባለ ድንጋጤ ተውጬ አድምጬዋለሁ፤ ግና ተሳዳቢው የክልሉ አስተዳዳሪ ይሆናል ብዬ አላሰብኩም ነበር፤ የንግግሩ ይዘት ከሞላ ጎደል እንደሚከተለው ይጠቃለላል፡-

‹‹….የአማራው ህዝብ በቅድሚያ እንዳይሰደድ ለማድረግ ስራ እየተሰራ ነው፣ ነገር ግን ከተሰደደ በሁዋላም ቢሆንም ሰንፋጭ የሆነውን ትምክህተኝነቱን በመተው፣ ከሌላው ጋር መኖርን መልመድ አለበት፡፡ …የአማራው ህዝብ ሰንፋጭ የሆነ ትምክህተኝነት የተጠናወተው በመሆኑ፣ በቤንሻንጉልና በሌሎችም ቦታዎች ለመሰደድ ምክንያት ሆኖታል። ….በባዶ እግሩ እየሄደ የሚናገረው ንግግር ግን መርዝ ነው። ይሄ መርዝ ንግግሩ አንድ የሚያደርግ አይደለም፡፡ …ከኢትዮጵያውያን ጋር አብሮ ለመኖር አማራው የትምክህት ለሃጩን ማራገፍ አለበት። ይሄ ለሃጭ ሳይራገፍ በጋራ መኖር አይቻልም። …ማንኛውም ስም ያወጣ ሙትቻ ፓርቲ ሁሉ መንገሻው አማራ ክልል ነው።ትምክህትን እንደ ምግብ ስለሚመገበው ነው። ያንን ምግብ እየተመገበ ያቅራራል።››

በእውነቱ ይህንን የተናገረው ፋሽስቱ ዱቼ ሞሶሎኒ አሊያም ሶማሊያዊው መሀመድ ዜያድባሬ ቢሆን ኖሮ፣ ቅኝ-ግዛት ያማለለው የፖለቲካ ፕሮፓጋንዳ አድርጎ ማለፍ ይቻል ነበር፤ ግን የዚህ ልብ ሰባሪ ቃላት ባለቤት የክልሉ አስተዳደሪ አለምነው መኮንን ነው፡፡ ዳሩ እርሱስ ቢሆን ማንን እየሰማ አደገና ነው! ምክንያቱም የቀደሙት የብአዴን ሰዎች የወከሉትን ዘውግ ሲረግሙና ሲያንቋሽሹ መታዘባችን የትላንት ክስተት ነው፡፡ የታምራት ላይኔን ‹ሽርጣም ሲልህ የኖረውን ይሄን ነፍጠኛ አሁን ጊዜው ያንተ ነውና በለው› የሚለውን ሐረር ላይ የተሰማ እልቅቲ ነጋሪ አዋጅ ጨምሮ፤ የተፈራ ዋልዋ ‹አማራው በባዶ እግሩ እየሄደ፣ ስንዴ በሩ ላይ አስጥቶ በባዶ ሆዱ የሚፉልል ትምክህተኛ ነው› እስከሚለው ድረስ ያሉ በአደባባይ የተሰሙ ስድቦችን መጥቀስ ይቻላል፡፡

በዚህ ጉዳይ ላይ የመጨረሻ ምሳሌ ለማድረግ፣ እዚህ ሳምንት ድረስ በሬዲዮ ፋና እየተተረከ ያለ አንድ የጥላቻና ዘረኝነት አቀንቃኝ የሆነ መፅሀፍን ልጠቀስ (በነገራችን ላይ እንዲህ አይነቱን ለእርስ በእርስ ግጭት መነሾ የሚሆን፣ በክፋት፣ በተንኮል፣ በክበረ-ነክ ጭብጥ የተሞላን መፅሀፍ ርዕስ እዚህ ጋ ማንሳቱ አስፈላጊ ነው ብዬ አላምንምና አልፈዋለሁ)፡፡ ይህንን መፅሀፍ ደረሲው ዳንኤል ግዛው በእንግሊዘኛ ቋንቋ ያዘጋጀው ሲሆን፣ ወደ አማርኛ የመለሰው የብአዴን ታጋይና የበረከት ስምኦን ባለቤት ወንድም የሆነው መዝሙር ፈንቴ ነው፡፡

በርግጥ በምስጋና ገፁ ላይ እንደተጠቀሰው፣ እንዲተረጉመው ያዘዘውና መፀሀፉን የሰጠው ለአማርኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች ነፃነትና ክብር በዱር-በገደል ታግያለሁ የሚለን ራሱ በረከት ስሞኦን ነው፤ ውለታውንም እንዲህ ሲል ገልፆለታል፡-

‹‹…የምተረጉማቸውን እያንዳንዳቸውን ገፆች ከስር ከስር እየተከታተለ ያነባቸውና ያበረታታኝ ነበር፡፡ ያስጀመረኝ እሱ፣ ያስጨረሰኝም እሱ ነበርና ለአቶ በረከት ስምኦን ያለኝ ምስጋና እጅግ ከፍ ያለ ነው፡፡››

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝም ‹‹አስተማሪ፣ አስገራሚና መሳጭ›› ሲል በፃፈው የጀርባ ገፅ አስተያየት፤ ይህንን እንቶ ፈንቶ እና አንድ ብሔርን ለይቶ የሚያጠቃ ውጉዝ ድርሳን ከፍቅር እስከ መቃብር ጋር በአቻነት አስከማስመሰል ታብዮአል፡፡ ህላዊ ዮሴፍም ረቂቁን በማንበብና በማረም ከፍተኛ አስተዋፆ እንዳደረገ ተርጓሚው ተናግሯል፤ በአናቱም መዝሙር ፈንቴ መፅሀፉን ከመተርጎሙ በፊት በ‹‹ደርባ ሚድሮክ ሲሚንቶ›› ፋብሪካ ውጪው ተሸፍኖለት (የማሳተሚያ ዋጋውንም የቻለው ሼክ መሀመድ አላሙዲ ነው) አደረኩት በሚለው ጉዞ፣ አማራ ረግጦ፣ ቀጥቅጦ፣ ከሰው በታች ዝቅ አድርጎ፣ መሬታቸውን በመንጠቅ አሽከር አድረጎ… እንደገዛቸው የተተረከላቸው የማንጃ እና ማኛ ብሔረሰብ አባላት ወደ ሚገኙበት ደቡብ ኢትዮጵያ ሄዶ ሰፊ ጥናትና ምርምር ማድረጉን ከነገረን አኳያ (የእንግሊዘኛውን ቅጂ ማግኘት አልቻልኩም) መፀሀፉ ቃል በቃል የተተረጎመ ነው ብሎ መቀበሉ ይቸግራል፡፡ ራሱም ቢሆን የፃሀፊው ተደራሲያኖች አሜሪካውያን መሆናቸውን ጠቅሶ ‹‹አቀራረቡን ኢትዮጵያዊ ለማድረግ ብዙ ጥረት አድርጌያለሁ›› ማለቱን ስናስተውል ከተርጓሚነትም ወሰን ተሻግሮ ተጉዟል ብለን እንድናምን ከመገፋታችንም በላይ፣ እነበረከት ስምኦን በአማራው ላይ ያላቸውን ያደረ ጥላቻ ለማንፀባረቅ የተጠቀሙበት ሊሆን ይችላል ብለን ለመጠርጠር እንገደዳለን፡፡

እንግዲህ ብአዴን ማለት፣ ከጉምቱ መሪዎቹ ጀምሮ የክልሉን ነዋሪ ‹‹ቀጣይ ነፃ አውጪያችሁ ነኝ›› የሚለውን ነውረኛውን አለምነው መኮንን ጨምሮ፣ ይህን መሰል በተዋረደ ስብዕና የሚበየኑ ምስኪን ፍጥረቶች የተሰባሰቡበት ድርጅት ነው፡፡ መሰረታዊው ጥያቄ ታዲያ፤ ለዚህ ሁሉ ሰቅጣጭ ሁኔታ፣ የክልሉ ነዋሪ የሆነው የአማርኛ ቋንቋ ተናጋሪ ዝምታ ምን ድረስ ይሆን? የሚለው ይመስለኛል፡፡

መልክዓ-ሌንጮ

ሌላኛው ሰሞነኛ ጉራማይሌ የፖለቲካችን ገፅ አንጋፋውን የኦሮሞ ልሂቅ ሌንጮ ለታን የተመለከተው ርዕሰ-ጉዳይ ነው፡፡ ኦነግን በመመስረትም ሆነ ፖለቲካዊ ቁመና ይዞ ህልው እንዲሆን ከዮሀንስ ለታ በላይ ማንም የለፋ እንደሌለ ይነገራል፤ ዮሀንስ ከጓዶቹ ጋር ተባብሮ ድርጅቱን ሲመሰርት ካነገበው አጀንዳ አኳያ ያለውን ተዛምዶ ገልፆ ባይነግረንም፣ ከልጅነት እስከ ጎልማሳነት ይታወቅበት የነበረውን መጠሪያ ስሙን ‹ሌንጮ› በሚል ቀይሮታል፡፡

ኦነግ እስከ 1983 ዓ.ም ድረስ የሻዕቢያ እና የህወሓትን ያህል ባይሆንም ያለፈውን ስርዓት ለመቀየር የጠመንጃ ትግል አድርጓል፡፡ ከዚህም አኳያ ይመስለኛል የመንግስቱ ኃይለማርያም አስተዳደር ግብዓተ-መሬት መፈፀሙ የቀናት ጉዳይ ብቻ እንደሆነ በታመነበት ወቅት በሀገረ እንግሊዝ፣ ሰሞኑን ‹ባድመን ለኤርትራ ስጡ› እያለ በሚወተውተን ኸርማን ኮህን አርቃቂነት በተዘጋጀው የለንደኑ ኮንፍረንስ ከሁለቱ ድርጅቶች ጋር የተቃውሞውን ፖለቲካ ወክሎ እንዲገኝ የተደረገው፡፡ ኋላም የታመነው ደርሶ አገዛዙ ሲወድቅ ኦነግም የሽግግር መንግስቱ መስራች አባል ሆኖ የመተዳደሪያ ቻርተሩን ዋነኛ አዕምዶች (የመሬት የመንግስት ባለቤትነት፣ የመገንጠል መብት እና ቋንቋ ተኮሩን ፌደራሊዝም) ከማርቀቅ ባለፈ እስከ 1984 ዓ.ም የመጨረሻ ወራት ድረስ የሥልጣን ተቋዳሽ ቢሆንም፣ ኢህአዴግ ባደረሰበት ጫናና ግፊት ሥልጣኑን ለቆ ተመልሶ ወደ በረሃ መግባቱ አይዘነጋም፡፡

ግና! ይህችን ለብዙ አስርታት በታጋዮቹ ስትማተር የነበረችውን የኦነግ የመኸር አንዲት ዓመትን ተከትሎ፣ በኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች ላይ መውረድ የጀመረው የመከራና የዕልቂት መዓት ዛሬም ድረስ አላባራም፡፡ እስከዚህች ቀንም እልፍ አእላፍ ንፁሃኖች በኦሮሞነታቸው ብቻ አስከፊውን የቃሊቲ ማጎሪያ ጨምሮ በተለያዩ ገሀነም-መሰል እስር ቤቶች የምድር ፍዳቸውን እየተቀበሉ ነው፡፡ በደርግ ዘመን የኤርትራ ነዋሪዎችን ‹‹ሻዕቢያ››! በማለት በአደባባይ ገድሎ መሄዱ ቀላል የነበረውን ያህል፣ ኢህአዴግም ሃያ ሁለቱን ዓመታት ሙሉ በኦሮምኛ ተናጋሪዎች ላይ ተመሳሳዩን ታሪክ ደግሞታል፡፡ የነገይቱን ኢትዮጵያ ህልውና በሚያጠይቅ ሁኔታም በግዙፉ ቃሊቲ ‹የእስር ቤቱ ቋንቋ ኦሮምኛ ነው› እስኪባል ድረስ ያለ አሳማኝ ክስ እያነቀ ግቢውን እንዲያጥለቀልቁት አድርጓል፡፡ የዚህ ሁሉ መነሻ ሰበብ የእነሌንጮ ለታ ድርጅት መሆኑ አይካድም፡፡

ኦነግ ከ1980ዎቹ መጨረሻ ወዲህ ለስርዓቱ አስጊ እንዳልነበር እና ይዞታውን ከባሌ ወደ አስመራ እና ሚኒሶታ ማዘዋወሩን፣ በስሙ ለተፈፀመው ዕልቂት ቀማሪና አዛዡ ህወሓትም ሆነ አስፈፃሚው ኦህዴድ ጠንቅቀው የሚያውቁት ቢሆንም፤ ‹‹በስመ-ኦነግ›› ከሚፈነዱና ከሚከሽፉ ፈንጂዎች ጋር እያያዙ የክልሉን ተወላጆች የጥቃት ኢላማ ማድረጉ መደበኛ መንግስታዊ ስራ ከሆነ ሁለት አስርታት ተቆጥረዋል፡፡ የዚህ መነሾም የህወሓት ኦሮምኛ ተናጋሪ ክንፍ ከሆነው ኦህዴድ ይልቅ፣ በኃይል የተገፋው ኦነግ በብዙሀኑ ልብ ማደሩ ያነበረው ፍርሃት አንዱ ሲሆን፤ ሌላው ደግሞ ኦህኮ እና ኦፌዴን (ባለፈው ዓመት ‹‹ኦፌኮ›› በሚል ስያሜ መዋህዳቸው ይታወሳል) ያላቸውን ቅቡልነት መጨፍለቅን ያሰላ ይመስለኛል፡፡

በዚህ የተቀነባበረ ጥቃትም ብዙዎች ለህልፈት፣ እልፍ አእላፍቶች ለእስርና ለስደት ተዳርገዋል፤ ቤተሰብ ተበትኗል፤ ህፃናት ያለ አሳዳጊ፣ አረጋውያን ያለ ጧሪ ቀርተዋል፡፡ እርግጥ ይሄ ጉራማይሌ አይደለም፤ አያሌ ማስረጃ ሊቀርብበት የሚችል ተጨባጭ እውነታ እንጂ፡፡ በአናቱም ይብዛም ይነስ የቀድሞ የኦነግ መስራችና የአመራር አባሉ ሌንጮ ለታ፣ ለዚህ ሁሉ ስቃይና መከራ የድርሻውን ያህል የታሪክ ተወቃሽ (ተጠያቂ) መሆኑ አከራካሪ አይደለም፡፡

የሆነው ሆኖ በሌንጮ ኦነግ ስም ለተገደሉት ገዳዮቻቸው ለፍረድ ሳይቀርቡ፣ የታሰሩት ሳይፈቱ፣ የተሰደዱት ሳይመለሱ፣ የፈረሱ ጎጆዎች ሳይቀለሱ፣ ሌላው ቀርቶ ከኢትዮጵያም አልፎ ከኬኒያ ‹ኦነግ› እያሉ አፍነው በመውሰድ ለእስር መዳረጉ (በቅርቡ በወህኒ ቤት ሕይወቱ ያለፈውን ኢንጂነር ተስፋዬ ጨመዳን እናስታውሳለን) ዛሬም ቀጥሎ እያለ ኦቦ ሌንጮ ለታ ‹‹የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ግንባር›› የተሰኘ አዲስ የፖለቲካ ድርጅት መስርቶ፣ ለሚቀጥለው ምርጫ እያሟሟቀ ከመሆኑም በላይ በቅርቡ ወደ ሀገር ቤት ገብቶ ታሪክ እንደሚሰራ የተናገረውን ማድመጣችንን ነው ለጉራማይሌ ፖለቲካ ማሳያ ያደረኩት (ሌንጮ ኦዴግን ከመሰረተ ጀምሮ ላለፉት በርካታ ወራት ‹‹ገብተን እንታገላለን›› ማለቱን ስንሰማ ከርመናል) በተያያዘም ሰውየው የኖርዌይ መንግስት የአፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ መሆኑን ስንጨምር፣ በአንድ ወቅት ራሱም ‹‹እዚህ ኖርዌይ ቁጭ ብዬ ምን እሰራለሁ?›› እንዳለው የአማካሪነቱን ከፍተኛ ደሞዝ ጭምር ትቶ ለመምጣት መወሰኑ፣ ቀጣይ ሚናው ላይ ያለውን የመተማመን ልክ ማየት እንችላለን፡፡ ርግጥ ሌንጮ ከ40 ዓመታት በፊትም የቅርብ ዘመዱ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ለታሪክ ትምህርት ወደ ጀርመን ለመሄድ አዲስ አበባ ላይ በተገናኙበት ጊዜ ‹አንተ ታሪክ ተማር፤ እኛ ደግሞ ታሪክ ሰርተን እንጠብቅሀለን› ማለቱ አይዘነጋም፡፡ ዛሬም ከአንደበቱ የሚወጡ ቃላቶች ስለታሪክ መጨነቁን ያመላክታሉ፡፡ ይሁንና ሌንጮ ‹ታሪክ መስራት› የሚለው የእነአባዱላ ገመዳን አይነት ወዶ-ገብት ከሆነ ሀፍረቱ ለሁላችንም መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡

በነገራችን ላይ ኦሮሚያን ለመደለል ሌንጮን በዝውውር የማምጣቱ ሥራ የተጀመረው በአቶ መለስ ዜናዊ ዘመን ነው፤ የዊክሊክስ ዘገባም እንደጠቆመው፣ መለስ ዜናው ‹‹ሌንጮ ማድረግ ያለበት እኔን ለማግኘት መሞከር ብቻ ነው፤ ይህን ደግሞ እንዴት ማድረግ እንዳለበት ያውቃል›› ማለቱን አስነብቦናል፡፡ እንዲሁም እ.ኤ.አ በ2007 ዓ.ም ኢንተር አፍሪካ ግሩፕ ባዘጋጀው፣ በአፍሪካ ቀንድ ሀገራት ሕገ-መንግስታዊነት ጉዳይ ላይ በተካሄደ ኮንፈረንስ፣ የቀረበውን የሌንጮ ለታን ጥናታዊ ፁሁፍ መከራከሪያዎችን በማብራራት ተጠምዶ የነበረው የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ ፕ/ር እንድሪያስ እሸቴ እንደነበረ ስናስታውስ፣ በሌንጮ የመምጣት ድርድር ውሳኔ ውስጥ የፕ/ሩን (የመንግስትን) የሰነበተ ሚና እንድንገምት እንገደዳለን፡፡ እርሱም ቢሆን ለመጀመሪያ ጊዜ ፊንፊኔ ላይ የታየው በ2004 ዓ.ም እንደሆነ ይነገራል፡፡ ከዚህ ሁሉ ጀርባ ደግሞ የአሜሪካ፣ ብሪታኒያ እና ኖርዌይ እጅ እንዳለበት ተሰምቷል፡፡ ባለፈው ዓመት ህዳር ወር መጀመሪያ ሳምንት ሌንጮና አባዱላ ገመዳ አሜሪካን ሀገር በሚገኝ አንድ ሆቴል ውስጥ አርፈው የነበረ መሆኑም የአጋጣሚ ጉዳይ አይመስለኝም፡፡

ኢህአዴግ ስጋት ላይ ከጣሉት የፖለቲካ ድርጅቶች ውስጥ ግለስብን ገንጥሎ ማማለልን ተክኖበታል፤ ከሶስት ዓመት በፊት መለክት ተንፍቶለት ወዶ የገባው አባቢያ አባጆቢር (ከኦነግ መስራቾቹ አንዱ የነበረ ሲሆን፣ ለእንግሊዘኛው ‹‹ዘ-ሪፖርተር›› ጋዜጣ በሰጠው ቃለ-መጠይቅ፣ የድርጅቱ የመጀመሪያ ፕሮግራም ላይ ስለመገንጠል የሚያወራውን አንቀፅ በወቅቱ ተቃውሜ ነበር ማለቱ ይታወሳል) ዛሬ ድምፁ አይሰማም፡፡ ከኦብነግ ጋርም ተደረሰ በተባለ ስምምነት የመጡትን ግለሰቦች፣ ድርጅታቸው አሁንም አፈመዝ ካለመድፋቱ አኳያ ስናየው ጨዋታው ዕቃቃ እንደነበር ይገባናል፡፡ በዚህ ሰሞን ደግሞ ዶ/ር መራራ ጉዲና ከፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች ጋር ሊወያይ ወደ ጀርመን አምርቷል፤ ሌንጮ ለታም አዳዲስ አባላትን ሊመለምል እዛው ጀርመን ይገኛል (ሁለቱ ጉምቱ የኦሮሞ ልሂቃኖች ተገናኝተው ይሆን?) በርግጥ ሌንጮ የጀርመን ቆይታውን ሲጨርስ፣ በሆላንድ ያቀደውን ተመሳሳይ መረሃ ግብር አከናውኖ በይፋ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመለስ ለጉዳዩ ከሚቀርቡ የመረጃ ምንጮቼ ሰምቻለሁ፡፡

ይሁንና እዚህ ጋ የሚነሳው ጥያቄ ሌንጮ ወደ ሀገሩ ለምን መጣ? የሚል አይደለም፤ እነበቀለ ገርባን የመሳሰሉ ፍፁም ሰላማዊ እና እጃቸው በንፁሀን ደም ያልጨቀየ ፖለቲከኞችን መታገስ ያልቻለ ስርዓት፣ ለሌንጮ የሚሆን ይቅር ባይነትን ከወዴት አገኘ? የሚል ነው፤ ሁለት አርፍተ ነገር የተናገረ ሁሉ ተለቃቅሞ እየታሰረ ሌንጮ ምን ተማምኖ መጣ? በኦሮሚያ ላይ የነገሡት እነአፄ አባዱላና ኩማ ደመቅሳስ ቢሆኑ ከሌንጮ አዲሱ ድርጅት ተነፃፅሮ የሚነሳባቸውን የቅቡልነት መገዳደር ለመጋፈጥ እንዴት ፍቃደኛ ሆኑ? ምናልባት መተካካት የሚባለው ይህ ይሆን እንዴ? ወይስ መረራ ጉዲና ‹‹የኦሮሞ ሕዝብ በቁመቱ ልክ ሥልጣን ይገባዋል!›› እንዲል፣ ሌንጮ ለታም በራሱ ቁመት የተቀነበበ ሥልጣን ቃል ተገብቶለት ይሆን? …የእነዚህና መሰል ጥያቄዎች ምላሽ ዛሬም በሙት መንፈስና በታመመ ሰው እንድትመራ በተፈረደባት ኦሮሚያ ላይ በቀጣይ ከሚኖረው ፖለቲካዊ አሰላለፍ ጋር መጋመዱ አይቀሬ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡

ከዚህ ባለፈ ‹‹ጀግናው›› ኢህአዴግ የሌንጮ ድርጅትን ኦፌኮን ወይም አንድነትን እንደመሳሰሉ ፓርቲዎች ነፃ ተቃዋሚ ሆኖ እንዲንቀሳቀስ ይፈቅድለታል ብሎ ማሰቡ እጅግ በጣም የዋህነት ይመስለኛል፡፡ በርግጥ ኦቦ ሌንጮ ከሳምንታት በፊት ለጀርመን ድምፅ ራዲዮ በሰጠው ቃለ-መጠይቅ ላይ፣ በቀጣዩ ምርጫ ለመሳተፍ ስለመወሰኑ ሲጠየቅ ‹‹ፖለቲካ በምርጫ በመሳተፍ ብቻ አይወሰንም፤ ሕዝቡን ማስተማርና ማንቃቱም አንዱ መንገድ ነው›› የሚል መንፈስ የያዘ መልስ ሰጥቷል፡፡ የሆነው ሆኖ ሌንጮ ለምርጫ ቅስቀሳ አሊያም ለንቃተ ህሊና ስብከት ፊቱን ወደ ኦሮሚያ ከማዞሩ አስቀድሞ የሚከተለው ጥያቄ ተጋፋጭ ተግዳሮት እንደሚሆንበት ይታሰባል፡- በሽግግር መንግስቱ ወቅት ሥልጣን ላይ የነበርክበትን ጊዜ ተከትሎ አንተን እና ኦነግን አምነው ከቤታቸው የወጡ ልጆቻችንን፣ ወንድሞቻችንን፣ አባቶቻችንን የት ጥለሀቸው መጣህ? ሰማዕታቶቻችንንስ በማን ስም እንዘክራቸው? … Akka dhufaa jirtu barree carraa garii (sihaaqunamu)

http://ecadforum.com/

posted Tseday Getachew

ህወሓት ከመለስ ጋር አብሮ ተቀብሯል (ክፍል ሁለት)

Tigray People Liberation Front Split

ከነፃነት አድማሱ
dalul@gmail.com

የሰው ልጅን ነፃነት የማይገባው ነፃ አውጪ!!

በትግራይ የህወሓት እኩይ ተግባር በቅርብ የተከታተሉት አንድ የሽሬ እንዳስላሴ አዛውንት እንዲህ በማለት በምሬት ይገልፁታል። “ደርግ ሰው ገድሎ በአደባባይ ይፎክር ነበር። ዛሬ ህወሓት ግን ሰው ገድሎ ልቅሶ ይደርሳል” ሲሉ የድርጅቱን እርኩስነት፣ አስከፊነትና የሰብኣዊ ፍጡር ባላንጣነት ካለፈው የደርግ አገዛዝ ጋር በማነፃፀር ቁጭታቸውን በትካዜ ሲናገሩ አጋጥሞኛል። የዛሬው ፅሑፌም ካለፈው ክፍል አንድ የቀጠለ ነው። በክፍል አንድ የተነሱ ዋና ዋና ጥያቄዎችም በኋላ በዝርዝር ለማስቀመጥ እሞክራለሁ። ለዛሬ ግን ቀደም ብዬ በክፍል አንድ የጀመርኩትን “አደናግረህ፣ አስፈራርተህ፣ አሸብረህ፣ ወገን ከወገኑ ጋር አናቁረህና ለያይተህ ግዛ” የሚለውን የህወሓት የደደቢት የደንቆሮ ፍልስፍናና መፈክር በሚመለከት አጭር ማጠቃሊያ በማከል ፅሑፌን እቋጫለሁ።

አዎ!! ህወሓት ለትግራይ ህዝብ ሶስት ጊዜ ገድለታል። መጀመሪያ ኤርትራን ከእናት ሀገርዋ ገንጥሎ ነፃ ለማውጣት በአስር ሽዎች የሚቆጠሩ የትግራይ ለወጋ ወጣቶች የሻዕቢያን ህይወት ለማዳን ሲባል በሳሕል በረሃ የአሞራ ሲሳይና የአቶ ኢሳያስ አፈ ወርቂ የስልጣን ማዳበሪያ ሆኖው እንዲቀሩ አድርጓል። ሁለተኛው አስከፊ ሞት ህዝቡ የባህር በሩን በመዝጋት ሉዓላዊነቱንና ብሄራዊ ጥቅሙን ከእጁ ነጥቀው ለማዕዳን አሳልፈው በመስጠት በህዝቡ ደም ቀልደዋል። ሶስተኛው አሳፋሪው ሞት ደግሞ ህዝቡ “ሻዕቢያ ይወረናል” እያለ ሲጮኽ ጆሮ ዳባ በመስጠት እንደገና ተመልሶ በኤርትራ ዳግም እንዲወረር በማድረግ ብሄራዊ ክብሩን እንዲደፈር፣ ዳር ድንበሩንና አንጡራ ሀብቱን እንዲዘረፍ፣ እንደ ዓይደር ትምህርት ቤት የመሳሰሉትን ጨምሮ ዳግም የሐውዜን ዓይነት እልቂት እንዲፈጠር አድርጓል። በአጠቃላይ የትግራይ ህዝብ ለባዕድ ጅብ አሳልፈው በመስጠት ለኤርትራ ነፃነት የከፈለውን የወጣቶቹን መስዋእትነት ደመ ከልብ ሆኖ እንዲቀር ተደርጓል።

ይህ በዓይናችን ያየነው በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ ተሰምቶ የማይታወቅ ብሄራዊ ውርደት፣ ሐፍረትና የታሪክ ጉድፍ መሆኑን ማንም ሀገር ወዳድ ዜጋ ሊገነዘበውና ሊቆጨው የሚገባ ጉዳይ ነው። በአባቶቻችን ተጠብቆ የቆየውን ክብራችንና ዳር ድንበራችንን የባዕዳን ደላላ በመሆን ያስደፈረ፣ ያዋረደ፣ የቸረቸረና ይቅር የማይባል ሀገራዊ ክሕደት የፈፀመው በሻዕቢያ ጡጦ ያደገው ህወሓት መሆኑን በያለንበት ለልጅ ልጆቻችንም ሳይቀር መናገርና ማስተማር መቻል አለብን።

አዎ!! የትግራይ ህዝብ ችግር በዚህ ብቻ አላበቃም። ቀደም ሲል ደርግን አሸንፈው ወደ አዲስ አበባ ብሄራዊ ቤተ መንግስት ገብተው ስልጣናቸውን ለማጠናከርና ለማደላደል ህዝቡን እንደ መሳለል አድርገው ከተጠቀሙበት በኋላም ዛሬም ትግራይ የርስ በርስ መበላላት፣ ግድያ፣ ድብደባ፣ አድልዎ፣ ዝርፊያና ሕግ አልባ ድርጊቶችን የሚፈፀምባት የጥፋትና የጭቆና ሞዴል ሆና ትገኛለች። የንፁኃን ደም የስልጣናቸው መቋደሻና መናገሻ አድርገው የሚጠቀሙ የህወሓት ሰበው በላ ካድሬዎችና መሪዎቻቸው ህዝቡን በመናቅና በማንቋሸሽ “ብንደበድብ የት ትደርሳለህ?!! መሳሪያውና ነፍጡ እንደሆነ በእጃችን ነው። ከኛ በላይ ነፋስ እንጂ ሌላ ሀይል የለም። ረግጠን ብንገዛህና የፈለግነው ብናደርገህ ማን ያድናሃል?!! ከኤርትራም ሆነ ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር እንደሆነም አጣልተናሃል።!! ስለሆነም ወደድክም ጠላህም ከእጃችን አታመልጥም። ስለዚህ አርፈህ ተገዛ።!! አፍህን ያዝ!! በነፃ መናገር ማን አስተማረህ? …. እያሉ እንደ ህፃን ልጅ በአለንጋ ሲገርፉትና በአደባባይ ሲቀጠቅጡት ይገኛል።

ታዲያ!! ለዚህ ሚስኪን ህዝብ ጠበቃ፣ ደራሽና አለሁልህ ባይ ማን ይሆን?። ትግራይ ብዙ ጀግኖች እንዳልወለደች ሁሉ ዛሬ በባዕድ ወረራ ጊዜ እንኳን በምንም መልኩ ያልታየ ጉድ እያየን ነው። ሰዎች በገዛ ሀገራቸው ጠላት እየተባሉ በአደባባይ የሚደበደቡባት፣ በእስር ቤት ቁም ስቃይ የሚታይባት፣ ህዝቡ ባለቤትና አቤት የሚልበት የፍትሕ ቦታ አጥቶ በሆዱ እያለቀሰ የሚኖርባት ምድራዊት ሲኦልና የጭካኔ ሞዴል ሆና እስከመቼ ትቆይ? እውነት ለራሳቸው ነፃ ያልወጡ የሻዕቢያ ተላላኪ የሆኑት የህወሓት ማፍያ መሪዎች የትግራይ ህዝብ ነፃ አውጪ ናቸውን? ለሚለው ጥያቄ መልሱና ፍርዱ ለአንባቢዎቼ ትቻለሁ።

ይሁን እንጂ ለባዕድ የማይንበረከክ፣ ጀግናና አትንኩኝ ባይ ህዝብ በላዩ ላይ ይህ ሁሉ ግፍ ሲፈፀምበት እየታየ ለምን ዝም ተባለ? በአካባቢው ሰው የለም ወይ? ያ ሁሉ ጀግና እየተባለ በትጥቅ ትግል ያለፈውና ራሱን ነፃ አውጪ ነኝ ሲል የነበረው ሰፊው የህወሓት ታጋይስ የት ገባ? የለውጥ ቀዳሚና ግንባር ቀደም መሆን የነበረበት የትግራይ ምሁሩና ተማሪውስ ምን ዋጠው? የትግራይ ተወላጅ ሆኖ የገዛ ወንድሙ በአደባባይ እንደ ውሻ በዱላ መደብደብስ የትግራይ ህዝብ ባህል ነው ወይ? ዛሬ በትግራይ ምድር ምን ዓይነት ትውልድ ነው እየተፈጠረ ያለው።? ችግሩ ለምን በትግራይ ያን ያህል የከፋ ሊሆን ቻለ።? ሌላው ኢትዮጵያዊስ በትግራይ አካባቢ ስለሚፈፀመው አስነዋሪ ተግባር ግንዛቤው ምን ያህል ነው።? የሚሉና ሌሎች ተዛማጅ ጥያቄዎችን በመጨመር በሚቀጥለው ሶስተኛ ክፍል ፅሑፌን አስር
ነጥቦችን ያካተተ ዝርዝር ሓተታ ይዤ እቀርባለሁ። በቸር ሰንብቱልኝ!!

http://ecadforum.com/

posted by Tseday Getachew

የነጻነት ትግል መሰዋእትነት ብእርም ብቻ አይደለም ተግባርም እንጂ!

ዮሴፍ ጸጋየ

Ginbot 7 Popular Force - GPF formed

የጽሁፌ መነሻ Ato ያሬድ ሃይለ ማርያም ወረድ ብሎ ደግሞ የማይቀረው ማእረግ ያለበት ለ ሰባት አመት በኢትዮጵያ የሰበአዊ መብት ምክርቤት የሰራ በወያኔ ግፍ ከሚወዳት ሀገሩ በ97 አም ጭፍጨፋ የተሰደደ ከፈለጋችሁ ደግሞ በአውሮፓ ህብረት የተናገረውን ምስክርነት ተመልከቱ ይላል። ይበጅ ብያለሁ! ከዚህ በፊት ለዳዊት ከበደ(አውራምባ ጋዜጠኛ) እልል በሉ ተብለን በኢሳት ቀርቦ እንዲሁም ሌሎች ሌሎች ተደርጎ አጨብጭበናል። ይህም ይሁን ዝናን የማይፈልግ ኢትዮጵያዊ ቁጥር በጣም ጥቂት ስለሆነ… ፕሮፌሰር…ዶክተር….ተመራማሪ…..ኢንጅነር…አንጋፋው ጋዜጠኛ…አንጋፋው አርቲስት… ወዘተ ብዙ ዝና አለን። ብዙ የነጻነት ታጋዮች፣ ወታደሮች የሉንም ቢኖሩም ጥቂትና እነሱንም ማጥፋት የተለመደ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል ባህሪያችን ነው። ምክንያቱም እነዚህ የነጻነት ታጋዮች ከዶክተሮቹ ከሰበአዊ መብት ተሟጋቾቹ መብለጥ የለባቸውም በሚል አናሳ አስተሳሰብ ነው። ቆብ ሌላ ተግባር ሌላ።

ወያኔ በሚሰጠን የቤት ስራ እየተዘናጋን ስራ ፈቶችን ሰብስቦ ትግሉ አንድ እርምጃ ወደፊት እንዳይራመድ እንባላ ዘንድ ማእረግ ባላቸው ሰዎች የምቀኝነትን መርዝ ማሰራጨት ይጀምራል። እኛ ደግሞ እንመቻቻለን። የነጻነት ትግል መንገዱን ወጣ ገባ ለማደረግ ያልተተባ፣ ያልተገራ ብእራችንን አንስተን “ግንቦት 7 ሆይ ፍረስ ወያኔ የጀመረን ይጨርሰን፣ ተዋርደን መገዛታችን እንቀጥል ዘንድ ወታደሮችህን ጋዜጠኞች አድርጋቸውና የዜና ሀተታ ይስሩልን” እንላለን።

እኔ ግን ከቻልን ትግሉን መቀላቀል ካልቻልንና እውነተኛ የኢትዮጵያ ህልውና እንዳትፈራርስ የምንፈልግ ከሆንን እሲት ገለል እንበል። ለወያኔ ብቻ ሳይሆን ለግንቦት ሰባትም፡፡ ማናችንም ቢሆን ብእርን አንሰተን ዌብሳየት ፈጥረን የምንታገለውን መሰዋእት ሳይሆን፤ እንደ እየሱስ ክርስቶስ በሞታቸው ድነትን፣ በደማቸው ነጻነትን፣ በአጥንታቸው ክብርን ሊመልሱልን ከበርሃ ማዶ ድቅድቅ ባለ ጨለማ የኢትዮጵያን ኤሎሄ ሰምተው ዳር ሳይሆን እሳት ላይ ያሉትን ጀግኖች ከእነ ችግራቸው በርቱ ከማለት ፈራርሱ ብሎ ማለቱ ማን ነኝ እኔ ማን ነው እሱ? እንበል እኔ ማጨብጨብ ደክሞኛል።

ስለዚህ ጸሃፊውና ብእሩ ምነው በዴሞክራቲክ በተባለው የወያኔ ግሩፕ ላይ አተኩሮ ሀገራችንን አደጋ ውስጥ የከተታትን ‘እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይበቅል’ ያለቸውን አህያ ነጭና ጥቁር አሊያም ቢጫ መሆኗን በካበቱት ልምዳቸው ለምን አላዩልንም ወይስ ይሄን አይጋ ፎረም ላይ አገኘዋለሁ?

በአኬልዳማ ድራማ ወያኔ ይህንን ጸሃፊው አሁን ያሉንን “የብዙ ወጣት ኢትዮጵያዊያኖችም ሕይወት በዚህ መያዣና መጨበጫ በሌለው የግንቦት 7 ቅዥት ተደናቅፏል” የሚለውን ዜማ ደጋግመን ሰምተናል። አብዛኞቻችን አይ ወያኔ እና ኢቲቪ ብለን እሰየው ግንቦት 7 በርቱ ወያኔ እንቅልፍ አጥቶ ሌሊት እየተነሳ ድራማ መስራት ጀምሯል አልን፤ ደገፍናቸውም። ታዲያ ወያኔና አጫፋሪዎቹ በደነገጡ ቁጥር ስራ ሳይሰራ ይቅር? ኧረ ግንቦት ሰባቶች ይህን ሰምታችሁ ቅር እንዳትሰኙ። በአማራው ፕሬዝዳንት ለሃጫም አማራ፣ ማንነቱን የማያውቅ ጫማ የሌለው ህዝብ፣ በሶማሊያው ፕሬዝዳንት አማራው ና ኦሮሞው እንዳየተባበሩ ትግሬውን ውደዱ፣ ከደቡብ ደግሞ አማራውን አስወጡ፣ ዋልድባን አፍርሱ… ዜጎቻችን ህገ-ወጥ ናቸው በሳውዲ ይገደሉ… እኮ የትኛው ይሆን ግንቦት 7 ፈጽሞት እንታገለው የምንለው? ኧረ ጎበዝ ማንነው የምንታገለው? በዳዩን ወይስ ተበዳዩን?

በርግጥ ነው ዝና የሚፈልጉ ሰዎች ወይም እኔ ያልኩት ካልሆነ የሚሉ ሰዎች ብእራቸውን አንሰተው አንዴ ስለ ግንቦት 7 የውጪ ፖሊሲ ሌላ ግዜ ደግሞ ስለ መከረኛው የህዝብ ልሳን “ኢሳት” ላይ መጎንተራቸው አልቀረም። ይህም ባልከፋ የአጻጻፉ ዘይቤ ወይም የትረካው አጨራረስ ግን ምን አለበት አንድ ሆነን እንደ ግንቦት 7 መረር ብለን “ታላቁን’ ህወሃት እንጥለው ዘንድ አመስግነው ቢዘጉት፤ ከፈቶ ከማበላሸት ይልቅ።

ልጨርስ “ነፃነትን የማያውቁ ነፃ አውጪዎች’ መሆን ይከብዳል። ስለዚህ በእኔ እምነት ግንቦት ሰባት የሚባለውን ሁሉ እያዳመጠ ሙያ በልብ ብሎ እንደሚሰራ አልጠራጠርም። ዶክተሮችም፣ ፕሮፌሰሮቹም፣ ኢንጅነሮችም፣ ወታደሮቹም አሉት ለየት ከሌላው የሚያደርጋቸው ማእረጋቸው ሳይሆን ለተነሱለት አላማ መጠመዳቸው ለተግባራዊ ስራ መፍጨርጨራቸው ነውና ተግባርን እናስቀድም፤ ከዛ ደግሞ እንተቻቸው። ትችት ጥሩ ነው ግን ከቅንነት ጋር ሲሆን ይጠቅማል፡፡ ስለዚህ ጠላታችን ወያኔ ነው!!! ብእራችን፣ ገንዘባችን፣ ጉልበታችን ሁሉ ለነጻነት ለሚደረጉ እልህ አስጨራሽ ትግል የሚረዱ ጋሻዎች ይሁኑን እላለሁ።

ህዝባዊ ሃይሉም በርታ! የማንችል ደግሞ አምላክ ጩኸታችን ሰምቶ ሀገራችንን የሰላም የደስታና የነጻነት ሃገር ያድርግልን ዘንድ እንጸልይ። የምንችል ደግሞ አንድ ሁነን ትግሉ ውስጥ እንግባና እንደህዝባዊ ሃይሉ እምቢ ለነጻነቴ፣ ለሀገሬ እንበል!!! ነገር ግን እምቢ ለወሬ……..
ዮሴፍ ጸጋየ kassa.yoseph@gmail.com

http://ecadforum.com/

posted by Tseday Getachew

ብሄሬ ኢትዮጵያዊነት ነዉ

– ግርማ ካሳ

ከበደ ካሳ የሚባሉ አፍቃሪ ኢሕአዴግ ግለሰብ “አንዳንድ ሰዎች «ብሄር ..?» ተብለው ሲጠየቁ «ኢትዮጵያዊ!!!…» እያሉ የሚመልሱት፣ የራሳቸዉን ማንነት የኢትዮጵያ ማንነት አድርገው ያስቀመጡና በራሳቸው ማንነት የሌሎቹን ለመጨፍለቅ የሚያልሙ – የቅዠት ታንኳ ቀዛፊዎች ናቸው…. ተዛብታችሁ ሌላንም ለማዛባት ለምትፈልጉ ሁሉ ኢትዮጵያዊነት ዜግነት እንጂ ብሄር አይደልም። ኢትዮጵያ ሃገር እንጂ የአንድ ሕብረተሰብ ክፍል መለያ አይደለም።” የሚል አባባል ፌስቡክ ላይ ለጥፈው አነበብኩ።
በአንቀጽ 39 ንኡስ አንቀጽ 5 ላይ የኢትዮጵያ ፌዴራል ሕገ መንግስቱ እንዲህ ይላል ፡

“በዚህ ሕገ መንግስት ዉስጥ «ብሄር፣ ብሄረሰብ፣ ሕዝብ» ማለት ከዚህ ቀጥሎ የተገለጸዉን ባህርይ የሚያሳይ ማህበረሰብ ነዉ። ሰፋ ያላ የጋራ ጠባይ የሚያንጸባርቅ ባህል ወይም ተመሳሳይ ልምዶች ያላቸው፣ ሊግባቡበት የሚችሉበት የጋራ ቋንቋ ያላቸው፣ የጋራ ወይም የተዛመደ ሕልዉና አለን ብለው የሚያምኑ፣ የስነ-ልቦና አንድነት ያላቸውና በአብዛኛዉ በተያያዘ መልክአ ምድር የሚኖሩ ናቸው»

እንግዲህ እዚህ ላይ እናስተዉል። ለብሄር የተሰጠው ትርጉምና ለብሄረሰብ የተሰጠው ትርጉም አንድ አይነት ነዉ። በአጭሩ ብሄር ማለት ብሄረሰብ ማለት ነዉ በሕገ መንግስቱ መሰረት።

ብሄር በእንግሊዘኛ ኔሽንስ ማለት ነዉ። «ዩናይትድ ኔሽንስ» ስንል የተባበሩት መንግስታት (የተባባሩት አገሮች ማለታችን ነዉ) ። እንደሚገባኝ ኢትዮጵያ እንጂ፣ ኦሮሞ፣ ወይንም፣ ትግሬ ወይንም ወላይታ የተባበሩት መንግስታት አባል አይደሉም።
«ብሄር» የሚለዉን ቃል የመጀመሪያ አመጣጥ ስንመለከት ፣ ከግእዝ የተወሰደ እንደሆነ እንረዳለን። ትርጉሙም በግእዝ አገር ማለት ነዉ።

ስለዚህ ኢሕአዴግን እና ኦነግ በሕገ መንግስቱ ብሄር የሚለዉን ቃል ያኔ የወሸቁት፣ ኢትዮጵያን እንደ አንዲት አገር ሳይሆን የተለያዩ የአገሮች ስብሰብ እንደሆነች ለማሳየት፣ በፈለጉ ጊዜ ደግሞ ከኢትዮጵያ ለመለየት አማራጭ እንዲኖራቸው ከመፈለግ የተነሳ ነዉ።
ፕሮፌሰር ተኮላ ሃጎስ ደግሞ ብሄር ብሄረሰብና ሕዝብ የሚለውን ለምን ሕገ መንግስቱ ዉስጥ እንደገባም ሲጽፉ የሚከተለዉን ነበር ያሉት፡

“The phrase “the nations, nationalities and peoples” thus found in the Ethiopian Constitution is a legacy from the writings of immature and juvenile diatribe of badly educated and socially disfranchised and radicalized students of Haile Selassie I University of the 1970s. It is the ersatz voice of Meles Zenawi forcing himself through the 1995 Constitution on the People of Ethiopia his narrow and ignoramus ideas on the history of Ethiopia and the process of nation building”

ስለዚህ «ብሄርህ ምንድን ነዉ ?» ተብሎ አንድ ሰው ሲጠየቅ «ኢትዮጵያዊነት» ብሎ ከመለሰ፣ በትክክለኛዉ የግእዝ አተርጓጎም እና በአለም አቀፍ ማህበረሰብ ዘንድ ብሄር የሚለው ቃል ያለው አጠቃቀም አንጻር፣ ትክክለኛ መልስ ነዉ።
«ብሄረሰብህስ ምንድን ነዉ ? » የሚል ጥያቄ ቢነሳስ ?

አንድ መርሳት የሌለብን ነገር አለ። አብዛኛዉ ኢትዮጵያዊ የተደባለቀ ነዉ። ሰሜን ጎንደና ሰሜን ወሎ ከሄዳችሁ ትግሪኛ ተናጋሪዉና አማርኛ ተናጋሪዉ ተደበላልቋል። ኦሮሚያ ዉስጥ በሸዋ፣ በሰሜን እና በምስራቅ ወለጋ..፣ አማራዉ ክልል ደግሞ በወሎ ፣ ኦሮሞኛ ተናጋሪው ከአማርኛ ተናጋሪው ተደባልቋል። በምስራቅ ሃረርጌና በባሌ ደግሞ ሶማሌዉና ኦሮሞዉ የተደባለቀበትም ሁኔታ አለ። በደቡብ ክልል ከሄድን፣ ወላይታዉ ከሲዳማው፣ ከንባታዉ ከሃዲያዉ …ሁሉም ተበራርዟል። ስለዚህ በአሥር ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዉያን የብዙ ብሄረሰቦች ድብልቅ ናቸው። በመሆኑም «ብሄረሰብህ ምንድን ነዉ?» ተብለው ሲጠየቁ እዚም እዚያም በመሆናቸው፣ ለመመለስ ይቸግራቸዋል። ስለዚህ በአጭሩ በብሄረሰባቸው ወይንም ዘራቸው ሳይሆን በኢትዮጵያዊነታቸው መለየትን ይመርጣሉ። ከነዚህ ሰዎች መካከል አንዱ እኔ ነኝ።
አቶ ከበደ፣ ኢትዮጵያዊያን፣ ብሄራችን ኢትዮጵያዊነት ነው ማለታቸው፣ የሌሎችን ማንነት ለመጨፍለቅ እንደመሞከር አድርገውም ወስደዉታል። አንድ ሰው «ኦሮሞ ነኝ፣ ትግሬ ነኝ ወዘተረፈ » የማለት መብቱ ከተከበረለት፣ ሌላው «አይ እኔ በዘሬ መለየት አልፈልግም፣ በኢትዮጵያዊነቴ ነዉ መለየት የምፈልገው » ካለ የርሱስ መብት ለምን አይከበርለትም ? ኦሮሞ፣ ወይም ትግሬ ፣ ወይም አማራ ያለመባል መብቱ መጠበቅ የለበትምን?

በኢሕአዴግ መንግስት፣ ይሄ መሰረታዊ መብት እየተጠበቀ አይደለም። እያንዳንዱ ዜጋ፣ እነርሱ ብሄር ብሄረሰብ የሚሉት አንዱ የዘር ሳጥን ዉስጥ መግባት አለበት። ያ ካልሆነ መታወቂያ እንኳ ማግኘት አይቻልም።

እንግዲህ ይሄንን ነዉ የምንቃወመው። «ለአገራችን የሚያዋጣዉ ዘር ላይ ማተኮር ሳይሆን፣ሥራ ላይ ማተኮር ነዉ። መመዘን ያለብን በዘራችን ሳይሆን በስራችን መሆን አለበት» እያልን ነዉ።
አፋን ኦሮሞ፣ ትግሪኛ፣ ጉራጌኛ፣ ሃምባሻ፣ ቆጮ ….በተለያዩ የአገራችን ግዛቶች ያሉ የተለያዩ ባህሎች፣ ቋንቋዎችን ፣ ምግቦች …ሁሉም «ኢትዮጵያዊነት» ናቸው። ሁሉም የኢትዮጵያ መገለጫዎች ናቸው። ኢትዮጵያ አንድ ወጥ አይደለችም። የተለያዩ ባህሎችን ፣ ቋንቋዎች፣ በአጭሩ የተለያዩ ብሄረሰቦች ያሉባት አገር ናት። ቢራቢሮዎችና አበባዎች የተለያዩ ቀለማቶቻቸው ዉበታቸው እንደሆነ፣ የኢትዮጵያም ዉበቷ ብሄረሰቦቿ ናቸው።

ግርማ ጌታቸዉ ካሳ
ዘብሄረ ኢትዮጵያ ( የዶር ፍቅሬ ቶሎሳን አባባል ልዋስና)

http://www.zehabesha.com/

posted by Tseday Getachew

“ስለአጼ ቴዎድሮስ እና አጼዮሐንስ መዝፈን የሚቻለው እነርሱ የሞቱለትን መሬት አሳልፈን ካልሰጠን ነው” – ኢንጂነር ይልቃል (ቪድዮ)

ባለፈው እሁድ በጎንደር ሰማያዊ ፓርቲ በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የፓርቲው ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት በተለይ ለወጣቶች ልብ የሚነካ ንግግር አድርገዋል። በንግግራቸው ከእንግዲህ በኋላ ስለአጼ ቴዎድሮስ እና አጼ ዮሐንስ መዝፈን የሚቻለው እነርሱ የሞቱለትን መሬት አሳልፈን ካልሰጠን ነው” ሲሉ ተደምጠዋል። ቪድዮውን ይከታተሉት።

posted by Tseday Getachew

በኢትዮ-ሱዳን ድንበር ዙሪያ የቴሌኮንፍረንስ ጥሪ ለመላው ኢትዮጵያውያን

ሸንጎ በኢትዮ-ሱዳን ድንበር ዙሪያ ሕዝባዊ ውይይትና ገለጻ ለማድረግ የፊታችን እሁድ ፌብሩዋሪ 9 ቀን 2014 ቴሌኮንፈርንስ ጠርቶ ማንኛውም ስለድንበሩ ያገባኛል የሚል ኢትዮጵያዊ እንዲገኝ ጥሪውን አቅርቧል። የጥሪው ወረቀት የሚከተለው ነው፦

https://i0.wp.com/www.zehabesha.com/amharic/wp-content/uploads/2014/02/shengo-forum.jpg

posted by Tseday Getachew

ስልክ ጠላፊው ሰላይ “ጋዜጠኛ”

በማህሌት ነጋ (ሲያትል)

ከሁሉ የእኔን ቀልብ የሳበው የቀጂው ማንነት ነበር። ለማጣራት ያደረኩት ጥረት ብዙም ግዜ አልፈጀብኝም። አበበ ገላው በዚሁ “ሊክድ” በተባለው ቅጂ “እኔ ከሞትኩም እንደ ሃየሎም መጠጥ ቤት በከንቱ መሞት አልፈልግም። መሞት የምፈልገው ለአላማ ነው ይላል።” በዚህ ግዜ አንድ ሳቅ ይሰማል። የኢያጎ ሳቅ። ዳዊት ከበደ ስለመሆኑ ብዙም አልተጠራጠርኩም።

Dawit Kebede Awramba Times editor in restaurant

ሰሞኑን አንድ ሚስኪን ጋዜጠኛ ነኝ ባይ ከአንድ የከሰረ ፖለቲካኛ ጋር ቃለ ምልልስ ሲያደርግ በቪዲዮ ለቆ ስለነበር ለሶስት ደቂቃ ያህል ተምልክቼ ጭንቅላቴን በሃዘን እየነቀነኩ ዘጋሁት። እኔን ጨምሮ በርካቶች ድረ ገጾችን የምናስሰው መረጃ ፍለጋ እንጂ የከሰሩ ግለሰቦችን ደረቅ ወግ ለማዳመጥ እንዳልሆነ ለማንም ግልጽ ነው። በአንድ ወቅት ያዙን ልቀቁን ይሉ የነበሩት ሁለት ግለሰቦች የዛሬን አያድርገውና ኢትዮጵያዊያን እንደ ማንዴላ የነጻነት ታጋዮች አድርገው ያከብሯቸው ስለነበር ድምጻቸው የጎላ በራስ መተማመናቸው ከውስጣቸው ሞልቶ በአፋቸው ይገነፍል ነበር። ዛሬ ግን ድምጽ አጥሯቸው ቀልብ እርቋቸው ሲንሾካሾኩ ያየ ሁሉ እንደ እኔ ከንፈር መጦ የሁለቱን ምስኪኖች ወግ በግዜ ዘግቶ ወደ ስራው እንደሚመለስ ብዙም አያጠራጥርም።

“ምስኪኖች እነማን ናቸው?” እንደማትሉኝ እርግጠኛ ነኝ:: የአውራምባው ዳዊት ከበደና የኢዴአፓው ልደቱ አያሌው ጉዳይ መቼም አንገት ያስደፋል። ሁለቱም ጠላታቸው ወያኔ እንዳልሆነ እነርሱ እንደሌሎች “ጽንፈኛ” እንዳልሆኑ ሌሎችን ከሰው እራሰቸውን ከፍ ለማድረግ ሲጥሩ ላስተዋለ ጠበል የሚወስዳቸው ያጡ በሽተኞች መሆናቸውን ድርጊታቸው ይመሰክራል። ዲያስፖራውና የግል ጋዜጦች በተለይ የጋራ ጠላቶቻቸው ይመስላሉ። እንደው ለመንደርደሪያ እንጂ የዚህ ጹሁፍ አላማ የሁለቱ ምስኪኖች ወግ ስላልሆነ ወደ ቁም ነገሩ ልመለስ::

ሾተላዩ ሰላይ ዳዊትን ለመጀምሪያ ግዜ በአካል ያገኘሁት ወደ ሲያትል የዛሬ ሶስት አመት በመጣ ግዜ ነበር። አስተባባሪዎች መርጠን፣ ገንዘብ አዋጥተን፣ ድግስ ደግሰን፣ ሽልማት አዘጋጅተን ነበር የጀግና አቀባበል ያደረግንለት። ወቅቱ የብርድ እና የበረዶ ግዜ ስለነበር እኔም እንደሌሎች ይህንን “ጀግና ጋዜጠኛ” ለመቀበል ብዙ መስዋእትነት ነበር የከፈልኩት። በተለይ የኢትዮሜድያው አብርሃ በላይና ሼክስፒር ፈይሳ እንግዳውን ተቀብለው ቤታቸው ከማሳደር አልፈው ለዝግጅቱ ስኬት ያበርከቱት አስተዋስኦ ቀላል አልነበረም። ሰላዩ ጋዜጠኛ ግን አብርሃ በላይን አራክሶ፣ ሼክስፒር ፈይሳን ደግሞ ስምህን አጠፋለሁ ብሎ በማስፈራራት ከንቱነቱን ብቻ ሳይሆን የኢያጎ ባህሪውን ፍንትው አድርጎ አጋልጧል።

ይሁንና ኢያጎን (ዳዊትን) በቅርብ የሚያውቁት ሁሉ አትመኑት ማለታቸው አልቀረም። እውነት ለመናገር ዳዊት እነ ውብሸት ታዬ እና ርእዮት አለሙን በማሳሰሩ ድርጊት እጁ አለበት የሚል ሹክሹታ ከወደ አገር ቤት ሲናፈስ ማናችንም የዚህ ጎጠኛ “ጋዜጠኛ” ወዳጆች በቁም ነገር አልወሰድነውም። መቼም ሰው በምልካም ስራው ሲታወቅና ሲወደስ ምቀኛ እንደማይጠፋ ለማንም ግልጽ ነው። ስለዚህም ነበር ዳዊትን አትመኑት የሚለውን የአገርቤት መልእክት ማንም ትኩረት ያልሰጠው። አሁንም ስለዚያ ድርጊቱ ተጨባጭ መረጃ ስለሌለኝ ድርጊቱን ፈጽሟል አልፈጸም ለማለት ባልችልም ከጀርባ የመውጋት ጋህሪውን ለማስተዋል በመቻሌ አያደርግም ብዬ መከራከር አልችልም።

ዳዊት ተራ የሆኑ ጉዳዮችን ሁሉ የመቅዳት ባህሪ አለው። ሰው ሲጎርስ፣ ሲጠጣ፣ ሲናገር፣ ሲቀልድ (ከተቻለውም ሽንት ቤት ሲጸዳዳ) ቪዲዮና ፎቶ ማንሳት ድምጽ መቅዳት ይወዳል። በስውር የሚቀዳበት ሪኮርደርም ይዞ እንደሚዞር ውስጥ አዋቂዎች ይናገራሉ። ብዙ ሰው ግን የዳዊትን ድርጊት ከጋዜጠኝነት ስራው ጋር ስለሚያያይዘው ተንኮሉን አይጠረጥርም። ነገሩ ያልጠረጠረ ተመነጠረ መሆኑን ነው።

Dawit Kebede's brother besrat amareአሁን እንደምንሰማው ነዋሪነቱ በአሪዞና ፊኒክስ የሆነው የዳዊት ከበደ ታላቅ ወንድም ብስራት ከበደ የሚታወቀው በተመሳሳይ የመቅዳት ባህሪው ነው። በሁለቱ መካከል ያለው ልዩነት ብስራት ምንም ጭንብል ሳያጠልቅ አይኑን በጨው አጥቦ ስለሚንቀሳቀስ የህወሃት ታማኝ ካድሬና ሰላይ መሆኑ በስፋት ይነገራል። እርሱም
እንደ ወንድሙ የትርፍ ግዜ ስራው ስለሆነ እንኳን ፖለቲከኞችን እና ታጋዮችን በስካይፕም ይሁን በስልክ የሚያናግራቸው ሴቶች ምስልና ድምጽ ሳይቀር እንደሚቀዳ በጉራ ይናገራል፣ ለቅርብ ጓደኞቾም ያሳያል። እዚህ ላይ ግለሰቡን እምታውቁ ሴቶች ጠንቀቅ በሉ ማለት ሳያስፈልግ አይቀርም።

የኢያጎ ጩቤ ወደ ዲሲ ደዋውዬ እንዳጣራሁት ዳዊት ወያኔ አባረረኝ ብሎ ወደ አሜሪካ ፈርጥጦ ሲመጣ የኢሳት ሰዎችም የተቀበሉት በመልካም አይን ነበር። በተለይ ከሲሳይ አጌና፣ ከመሳይ መኮንን እንዲሁም አበበ ገላው ጋር መልካም ወዳጅነት ለማፍራት፣ አብሮ ለመጠጣትና ለመብላት ግዜ አልወሰደበትም። ለጋዜጠኝነት ስነምግባር እጨነቃለሁ የሚለው ይሄው ግለሰብ ወያኔ ጠለፍኩ ያለውን የዶ/ር ብርሃኑን የስካይፕ ውይይት በድህረ ገጹ ላይ በማውጣት የራሱ አጸያፊ ድርጊት መነጋገሪያ ሆኖ እንደ ነበር ይታውሳል። ዳዊት ከበደ በኢሳት፣ ግንቦት ሰባትን እና ዶ/ር ብርሃኑ ላይ በተከታታይ የሰራውን አሳፋሪ ግን ደግሞ የከሸፈ ፕሮፓጋንዳ ሁሉም ስለሚያውቀቅ መድገም አያስፈልግም። ከሁሉ የገረመኝ ሰሞኑን ዳዊት ኢያጓዊ የስለላ ስራውን ለማራቀቅ መሞከሩ ነው። ሞኝ እራሱን ያታልላል ነው ነገሩ።

ልክ እንደ ኢያጎ ዳዊትም ጩቤን በጀርባው ደብቆ ያመኑትን እና ያቀረቡት ሁሉ ላይ ከማሴር ቦዝኖ እንደማያውቅ ሙሉ በሙሉ ግልጽ ሆኗል። በቅርቡ ለመረዳት እንደቻልኩት በርግጥም የዛሬው ኢያጎ ዳዊት ከበደ መስዋእትነት ከፍሏል፣ መልካምነቱንም በስራው አስመስክሯል በማለት እንደ ትግል አጋር ያዩት ከነበሩ በርካታ ኢትዮጵያዊያን አንዱ ጋዜጠኛ አበበ ገላው ይገኝበታል። ለዚህም ምክንያት አንዱ ኢያጎ ከእስር ወጥቶ በሲፒጄ ሳይቀር ለፕሬስ ነጻነት ላበረከተው አስተዋጽኦ በታላላቅ የአለማችን ጋዜጠኞች ፊት በኒውዮርክ ቀርቦ ሽልማት ሁሉ መውሰዱ ነው። ይቺም ስኬት ለዳዊት ጥሩ ጭንብል ሆና ቆይታለች።

በወቅቱም ወያኔ ይገለኛል ያስረኛል እንጂ አገር ለቅቄ አልሰደድም ብሎ በየመድረኩ ሲደነፋ በእውነትም የጎልያድ ጠላት ቅዱስ ዳዊትን ነበር የመሰለን። ያሁሉ ተረት ሆኖ ወያኔ ሊያስረኝ ነው ብሎ አገር ጥሎ ሲፈረጥጥ አሜሪካ ያሉ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ ክብርና ፍቅር አልነፈጉትም ነበር። የእኛው ኢያጎ ግን ያን ሁሉ ክብር ትቶ በእኩይ ተግባሩ የነጻንት ትግሉን የሚጎዳና የህወሃት አንባገነኖችን በሚጠቅም እኩይ ተግባራት ላይ ለመሰማራት ግዜ አልፈጀበትም።

በቅርቡ ወያኔዎች ክፉውን ጎልያድ መለስ ዜናዊን በአለም መሪዎች ፊት አዋርዶና አስደንግጦ የመጨረሻና ወሳኝ ስንብት ላደረገለት ጋዜጠኛና አክቲቪስት አበበ ገላውን ለማስጠላት እንዲሁም ኢትዮጵያዊውን ለመከፋፈል በህገወጥ መንገድ የተቀዳ የግል የስልክ ንግግር አዛብተው፣ ቆርጠውና ቀጥለው በኢንተርኔት ላይ ለቀቁ። ይሄም የተለቀቀው በዳዊት ድርገጽ ሳይሆን በቀንዲል የወያኔ የፈስቡክ አቀንቃኝ ዳንኤል በርሄ አማካኝነት በሆድ አደሩ ሹምባሽ ከበደ ካሳ አቀናባሪነት ነው። ደግነቱ የተባለው ሁሉ ምንም ሚስጥር የሌለው ስለነበር እንዳሰቡት ሳይሳካላቸው እነርሱንው መሳለቂያ አድርጓቸዋል።

ከሁሉ የእኔን ቀልብ የሳበው የቀጂው ማንነት ነበር። ለማጣራት ያደረኩት ጥረት ብዙም ግዜ አልፈጀብኝም። አበበ ገላው በዚሁ “ሊክድ” በተባለው ቅጂ “እኔ ከሞትኩም እንደ ሃየሎም መጠጥ ቤት በከንቱ መሞት አልፈልግም። መሞት የምፈልገው ለአላማ ነው ይላል።” በዚህ ግዜ አንድ ሳቅ ይሰማል። የኢያጎ ሳቅ። ዳዊት ከበደ ስለመሆኑ ብዙም አልተጠራጠርኩም። ሳቁ በጣም የተለየች ውስጧ ሸፍጥና ተንኮል ያዘለች ነች። ዳዊትን ለሚያውቁት ወዳጆቼ አስተያየት ሳልሰጥ ይቺን አምልጣ ስትቆረጥ የወጣች ወሳኝ መረጃ አድምጣችሁ የማን ሳቅ እንደሆነ ንገሩኝ ብዬ በኢሜይል አያይዤ ላኩላቸው። አራቱም መልሳቸው አንድ ነው፣ የኛው ኢያጎ ዳዊት ከበደ።

ዳዊት በጣም አሳዘነኝ። ብዙ ተስፋ የጣልንበት “ጋዜጠኛና የነጻነት ታጋይ” እንዴት ከክብር ወንበሩ ወርዶ ቆሻሻ ትቦ ውስጥ ይወድቃል? ለነገሩ ከልብ ያልሆነ ነገር ሁሉ እራሱን መግለጡ አይቀርምና ዳዊትም ከልቡ ኢያጎ እንጂ ሌላ አልነበረም። በጣም ተምታቶበታል። እኛ ግን የበለጠ ነቃን። እነዳዊት ከበደ ግን ግራ እንደተጋቡ እንደሰካራም በየትቦው ውስጥ እየወደቁ ይገኛሉ። ተመስገን ደሳለኝ ከጥቂት ወራት በፊት “የፖለቲካ ስር ቁማርተኞች” በሚል የጻፈው አንጀት አርስ ጹሁፍ ትዝ አለኝ። ተመስጌን የጠየቀው መሰረታዊ ጥያቄ በእኔም አእምሮ ውስጥ ያቃጭላል። ለመሆኑ ወደ አገር ቤት ከአሜሪካ ልክ እንደ አመጣጡ ፈርጥጦ ያስመለሰው ጉዳይ የፕሬስ ነጻነት መሻሻሉና “የጽንፈኞችን” ፖለቲካ በመጸየፉ ነው ወይንስ ደግሞ ኢሳትን የማፍረስ እና በጸረ-ወያኔ ትግሉ ግንባር ቀደም ሚና ይሚጫወቱ ኢትዮጵያዊያንን ለማምታታትና ለመሰለል ስላላመቸው? መልሱ ግልጽ ነው።

ወያኔዊ ኢያጎነት በቀላሉ እንደማይለቅ ከዳዊት መማር ይቻላል። ዲሲ አካባቢ በቅርብ የታዘቡት እንደነገሩኝ ዳዊት ሁለት ነገሮች አብዝቶ ይወዳል፣ መጠጥና ሴት ማባረር። ከአገር ቤት ፈርጥጦ ዲያስፖራ የተቀላቀለው ዳዊት ሲነቃበትና ይሄ የሱስ ጥማት ሲያስቸገረው ፈርጥጦ እነአቦይ ስብሃት እና ሽመልስ ከማል ጋር ብርጭቆ ማጋጨት መጀመሩን ሰማን። ተመሳሳይ ላባ ያላቸው ወፎች አብረው ግር ይላሉ አሉ ፈረንጆች። አበው ሲተርቱ ግም ለግም አብረህ አዝግም እንዳሉት መሆኑ ነው። መልካም እድል፣ መልካም ቅምቀማ ብለናል ከወደ ሲያትል!!

http://ecadforum.com/

posted by Tseday Getachew

 

ደመቀ መኮንን ልምድ ያለው ውሸታም (ከሁኔ አቢሲኒያዊ)

(የዚህ ጽሁፍ ጸሀፊ በ2004 ዓ.ም የመምህራን ደመወዝ ጭማሪን አስመልከቶ በተነሳው ተቃውሞ መምህራኑን አነሳስተሀል ተብሎ ከመምህርነት ሙያው የተባረረ ነው)

ከሁኔ አቢሲኒያዊ

  • ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ 3481 መምህራን ከስራቸው ለቀዋል
  • አዲስ አበባ ውሰጥ በበርካት ት/ቤቶች በአንድ ክፍል ውስጥ ከ90 በላይ ተማሪ ይማራል
  • ልጁን በመንግስት ት/ቤት የሚያስተምር አንድም ባለስልጣን የለም
  • በስኳር ቴክኖሎጂ የተማረ የሰው ኃይል የለም ብለዋል አቦይ ስብሀት
  • ለየወረዳው ካድሬዎች እስከ 2500 የሚደርስ የደመወዝ ጭማሪ ተደርጓል
  • በስብሰባ ምክንያት ቅዳሜ ማስተማር ያስቀጣል

እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በርካታ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ ትምህርት አስተሳሰብን ብሎም ኑሮን ይቀይራል ብለው በማመን ልጆቻቸውን ወደ አሰኳላ በመላክ የማስተማር ከፍተኛ ፍላጎት ነበራቸው ለዚህም እንደምክንያት የሚያቀርቡት ልጆችን ማስተማር የነገ ህወታቸውን ማስተካከል ነው ብለው ስለሚያምኑ እና ትክክልም ስለነበሩ ነው ነገር ግን ባለፉት 23 ዓመታት የህወሀት ኢህአዴግ ዘመን ከጊዜው እና ካለው የህዝብ ቁጥር አንፃር የተማረ የሰው ኃይል ቁጥር ከፍ ያለ ቢሆንም ብዙሀኑ ህዝብ ግን ትምህርትን የሚማረው ነገ ተምሮ ምንም ተስፋ እንደሌለው ተረድቶ ነው፡፡

Ethiopian Minister Demeke Mekonnen

ደመቀ መኮንን

ከሰሞኑ ሀገራችን ኢትዮጵያ ትምህርት ለሁሉም በማዳረስ አቻ እንዳልተገኘላት የህወሀት ታማኝ አገልጋይ የሆነው ደመቀ መኮንን በቴሌቪዥን መስኮታችን ብቅ ብሎ ነግሮናል ወይም ዋሽቶናል፡፡

የዚህ ፅሁፍ ፀሀፊ ሀሳብ ኢትዮጵያ እውን ቁጥሩን አሳክታለች አላሳካችም ሳይሆን ኢትዮጵያ ያለችበትን ነባራዊ የትምህርት አሰጣጥን ማሳየት ነው፡፡

በአንድ ወቅት ሁሉንም አውቃለው የሚለው ስብሀት ነጋ በስኳር ቴክኖሎጂ ሀገሪቷ ውስጥ ምንም የተማረ የሰው ኃይል እንደሌለ ሰንደቅ ለተበላው ጋዜጣ ተናግሮ ነበር ነገር ግን ይህ የህዝቡ በስኳር ቴክኖሎጂ ተምሮ ያለመመረቅ ፍላጎት ሳይሆን የመንግስት የተሳሳተ የትምህርት ፖሊሲ በዘልማድ እና ገበያውን እንዲሁም ሀገራችን የሚያስፈልጋትን የተማረ የሰው ኃይል አይነት ካለማወቅ የሚመጣ ነው፡፡ በአሁኑ ሰዐት በርካታ ወጣት ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ኬሚስትሪ እና ፊዚክስ ተምረው እቤት ተቀምጠዋል ድህነታቸው ለህወሀት አሽከር ያደረጋቸው ወንድሞቻችን ደግሞ ኮብልስቶን እየሰሩ ይገኛሉ እነዚህ ወጣቶች ቀድሞውኑ የተሻለ የትምህርት ስርዓት እና ፖሊሲ ቢኖር ኖሮ አቦይ ስብሀት እንደሚሉን ምንም የተማረ የሰው ኃይል በሌለበት የስኳር ቴክኖሎጂ ተምረው እራሳቸውንም ሀገራቸውንም በቀየሩ ኖሮ፡፡

ደመቀ መኮንን እንደዛ ያለማፈር አፉን ሞልቶ የተናገረለት የሀገራችን የትምህርት ስርዐትን ለመታዘብ አዲስ አበባ የሚገኝ አንድ የመንግስት ትምህርት ቤት ጎራ ማለት አልያም መምህራኑን ማነጋገር በቂ ነው፡፡

በትምህርት የተሻለ ደረጃ ደርሳለች በምትባለው አዲስ አበባ በርካታ ት/ቤቶች ውስጥ በአንድ ክፍል እስከ 90 የሚደርስ ተማሪ ይማራል ይኸውም ተማሪው በትክክሉ ትምህርት አንዳያገኝ ብሎም መምህሩ እውቀቱን በአግባቡ እንዳያደርስ የሚያደርግ ነው ይህንንም ችግር ስለሚያውቁ ነው ሁሉም ባለስልጣኖች ልጆቻቸውን ወደ ውጭ ሀገራት ብሎም ከፍተኛ ክፍያ በሚያስከፍሉ ት/ቤቶች የሚያስተምሩት ነገር ግን ልጆቻቸው እንኳን እንዲማሩ የማይፈቅዱበትን የመንግስት ት/ቤቶች ሀገሪቷ እንደተቀየረች ማሳያ አድርገው ያቀርቡልናል፡፡

መንግስት ማለትም ህወሀት ከትምህርት ይልቅ የፖለቲካው ነገር ያንገበግበዋል ፡፡ በቅርቡ ለሁሉም የህወሀት ኢህአዲግ ተቀጣሪ የየወረዳው የፖቲካ ሹመኞች በሀገሪቱ ታይቶም ተሰምቶም የማያውቅ እስከ 2500 ብር የሚደርስ የደመወዝ ጭማሪ አድርጓል ከዚህ ቀደም በኑሮ ውድነቱ ተሰቃየን ሲሉ ከፍተኛ ዛቻ እና ከስራ ማባረር ለፈፀመባው መምህራን እና የመንግስት ሰራተኞች ትኩረት አለመስጠቱ ብሎም ደመወዛቸውን ለመጨመር አለማሰቡ ህወሀት ኢህአዴግ ከዜጎች በላይ ካድሬዎች የሚል ፅንሰ ሀሳብ ውስጥ መሆኑን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው፡፡

ት/ቤቶች በአሁኑ ሰዐት እንደበፊቱ ቅዳሜ እና እሁድ የማጠናከሪያ ትምህርት መስጫ ከመሆን ይልቅ የካድሬ መሰብሰቢያ ማዕከል ወደመሆን ተሸጋግረዋል ቅዳሜ ቀን ተማሪዎቹን የማጠናከሪያ ትምህርት የሚጠራ ማንኛውም መምህር ስብሰባ እንዳወከ ተቆጥሮ በት/ቤቱ ኃላፊዎች ከፍተኛ ሆነ ማስፈራሪያ እና ዛቻ ይደርሰዋል ይህንንም ተከትሎ በርካታ መምህራን መምህርነት ሙያን እንደስራ መፈለጊያ ይጠቀሙበታል፡፡ በቅርቡ ከአዲስ አበባ መምህራን ማህበር ለከተማው የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዲላሞ ኦቶሬ የቀረበው ማስረጃ እንደሚያሳየው ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ 3481 መምህራን ስራቸውን ለቀዋል፡፡

እንግዲህ ይህንን ነው ባለልምዱ ውሸታም ደመቀ መኮንን ለውጥ ብሎ የሚነግረን፡፡

http://ecadforum.com/Amharic/

posted by Tseday Getachew

ኢትዮጵያን ከቅርጫ ለማትረፍ

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

Ethiopia chop shop rez

የአሁኑ አስገራሚ ጊዜ ሸክስፒር፣ ጁሊየስ ቄሳር በሚለው ፅሁፉ ላይ ለተናገረው  አነጋገር ልዩ ትርጉም ይሰጠዋል፣ “ሰዎች የሰሩት ተንኮል ከመቃበራቸው በላይ ሀያው ሆኖ ይኖራል” ብሎ ነበር ሸክስፒር፡፡ በአሁኑ ጊዜ አቶ መለስ ዜናዊ በህይወት በነበሩበት ጊዜ ከሰሩት ተንኮሎችና ጭራቃዊነት የሞላው አስቀያሚ ተግባር ውርስ ጋር ፊት ለፊት ተፋጥጠን እንገኛለን፡፡ የኢትዮጵያ ሉዓላዊ የግዛት አካል ተቆርሶ እንደገና ለሽያጭ ለሱዳን ቀርቧል፡፡ ይህንንም ጭራቃዊነት ተንኮል የቀበሮ ባህታውያኑ “የድንበር ማካለል“ ብለው ይጠሩታል፡፡ እኔ ደግሞ ድንበር መቁረስ፣ መቆራረስ፣ መሽረፍ እና መሸራረፍ ብዬ እጠራዋለሁ፡፡ ባጭሩ ኢትዮጵያን  ለቅርጫ ማቅረብ እለዋለሁ… ደግሞ ለሰላሳ ቁርጥራጭ የመዳብ ዲናሮች!

እ.ኤ.አ በ2008 “የኢትዮጵያ ጋሻ“ ተብሎ በሚጠራው የሰሜን አሜሪካ የሲቪል ማህበረሰብ ስብስብ ጉባኤ ላይ በመገኘት የእናት አገር ኢትዮጵያን ሉዓላዊነት መጠበቅ በሚል ርዕስ ስሜትን የሚቀሰቅስ ንግግር አድርጌ ነበር፡፡

በዛሬዋ ዕለት እዚህ የተሰባሰብንበት ዋናው ምክንያት አቶ መለስ ዜናዊ እናት አገራችንን መቅን አሳጥተው ለመበታተን እንዲመቻቸው በበረሃ ሳሉ ነድፈው ያመጡትን ጭራቃዊ ዕቅድ እና ዕኩይ ምግባር ለማውገዝ እና ለማስቆም ነው፡፡ አቶ መለስ የአሰብን ወደብ አሳልፈው በሰጡበት ወቅት ዝምታን በመምረጣችን ወደብ አልባ የመሆንን ዋጋ ከፍለናል፡፡ እ.ኤ.አ በ1998 ባድመ ተወረረች፣ እናም የ80,000 ኢትዮጵያውያን ህይወትን የበላ መስዋዕትነት ተከፍሎ ጠላቶቻችን ከግዛታችን እንዲወጡ ተደረገ፡፡ ሆኖም ግን አቶ መለስ በብርሃን ፍጥነት ተገልብጠው የኢትዮጵያን አንጸባራቂ የጦር ሜዳ ድል ቀልብሰው የዲፕሎማሲያዊ ሽንፈትን በመጋት በእርቅ ሰበብ ስም ባድመን ለወራሪው ኃይል አሳልፈው ለመስጠት ስምምነት አደረጉ… (ዛሬ) በምዕራብ ኢትዮጵያ የሚኖሩ ወገኖቻችን በግልጽ እንደነገሩን የአያት ቅድመአያቶቻቸውን መሬት እና መኖሪያ ቤታቸውን ሳይቀር አቶ መለስ ለሱዳኑ አምባገነን [በዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት በወንጀል ለሚፈለጉት እና ከፍትህ ለማምለጥ እራሳቸውን በመደበቅ ተወሽቀው ላሉት] መሪ ኦማር አልባሽር አሳልፈው ለመስጠት በሚስጥር ስምምነት ፈጽመዋል…

ያንን ንግግር ካደረግሁ ከስድስት ዓመታት በኋላ እንኳን በሚያሳዝን ሁኔታ እናት አገራችንን ለመበታተን አቶ መለስ ከበረሃ ውስጥ ነድፈው ያመጡትን ጭራቃዊ ዕቅድ እኩይ ምግባር ለመቀልበስ ባለመቻላችን አዝናለሁ፡፡ አቶ መለስ አሁን በህይወት የሉም፣ ሆኖም ግን እኛን እንዲያጠፋ ጥለውት ከሄዱት ተንኮላቸው ስራቸው ጋር ፊት ለፊት ተጋትረናል፡፡ “መልካም ሰዎች ዝም ስላሉና ምንም ባላማድረ ጋቸው ይሆን ተንኮል የሚበረታው” የሚለው አባባል እውነታነት አለውን? በመጨረሻም ተንኮልና ጭራቃዊነት ድል ተጎናጽፏልን?

ኢትዮጵያ በአቶ መለስ ዜናዊ ቅርጫ መግባት

እ.ኤ.አ ዴሴምበር 2013 የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሆኑት ዓሊ ካርቲ የኢትዮጵያ እና የሱዳን ገዥ አካላቶች “ፋሻጋ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የነበረውን የድንበር አለመግባባት እና በሌሎች አካቢዎችም ያሉትን የድንበር ማካለል ስራዎችንም በሰላማዊ መንገድ ለማጠናቀቅ ስምምነት አድርገናል“ በማለት በግልጽ ተናግረዋል፡፡ ስለሁለቱ አገር መሪዎች አስመልክቶ ካርቲ እንዲህ ብለዋል፣ “የመጨረሻውን የማካለል ስራ ለመተግበር ታሪካዊ ስምምነት አድርገናል፡፡“ የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት በኢትዮጵያ እና በሱዳን መካከል ያሉትን “የድንበር ውዝግቦች” በማስመልከት ለሚቀርቡ አስተያየቶች ሁሉ ምንም ዓይነት ሀሳብ እንደማይቀበል ጠቅሶ ሲናገር፣ “በጠረፉ በተወሰኑ የወሰን ድንበር ነጥብ ቦታዎች ላይ“ በጣም ቀላል የሆኑ አለመግባባቶች ከመኖር በስተቀር ሌላ ቸግር እንደሌለ አስረግጠው ተናግረዋል፡፡

ባለፉት ሳምንታት የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት መምሪያ እንደ ዔሌ አንገቱን ብቅ ጥልቅ እያደረገ በድብቅነት እና ማደናገር በተላበሰ ስልት/strategy “የድንበር ማካለሉን ጉዳይ“ እና “መጠነሰፊ ጠቀሜታ“ አላቸው እያለ ከበሮ የሚደልቅላቸውን “የደህንነት ትብብር ስምምነት፣ የኢኮኖሚ፣ የግብርና፣ የትምህርት እና የባህል“ “የስትራቴጅክ ስምምነት ማዕቀፍ“ በማለት በሚጠራቸው ጉዳዮች ላይ እምነት እንዲያድርብን የፕሮፓጋንዳ ዘመቻዎችን በመሰለቅ ጊዜውን በከንቱ አሳልፏል፡፡

እ.ኤ.አ በ2001 “ለድንበር ውዝግቡ” ይሰጡ የነበሩት ምክንያቶች አሁን እየተሰጡ ካሉት ምክንያቶች ፍጹም የተለዩ ነበሩ፡፡ በዚያን ጊዜ የሱዳን ገዥ አካል እንደገለጸው የድንበር ማካለሉ ስራ አስፈላጊነቱ “የአልቃዳሪፍን ግዛት በሰሜን ኢትዮጵያ ከሚገኘው የትግራይ ግዛት ጋር ‘ለማልማት እና ለማቆራኘት‘ የሚል ነበር… ሁለቱ አካባቢዎች በጣም ለም የነበሩ ሲሆኑ፣ ከዚህም በላይ አልቃዳሪፍ ለሱዳን የዳቦ ቅርጫት ተደርጎ የሚቆጠር ነበር… ከአልቃዳሪፍ እስከ መቀሌ ያለው የመኪና መንገድ…እየተጠገነ እና ደረጃው ከፍ እየተደረገ ነው… የትግራይ ግዛት ከዚህ በመነሳት በዚህ በኩል ወደ ቀይ ባህር የሚያሸጋግረው ዕድል ስለሚያገኝ እና አልቃዳሪፍ ደግሞ ከፖርት ሱዳን ጋር የሚያገናኘው ስለሆነ ተቃሚ ይሆናል፡፡ በዚህም መሰረት ፖርት ሱዳን ለመቀሌ በኤርትራ ግዛት ከሚገኘው የአሰብ ወደብ እና በሶማሌ ግዛት ከሚገኘው የበርበራ ወደብ የበለጠ ቅርብ ትሆናለች…“ የሚል ነበር፡፡

እ.ኤ.አ በ2008 አቶ መለስ ዜናዊ ከሱዳን ጋር የተደረገውን “ስምምነት” አስመልክቶ በውሸት ባህር ውስጥ እየተንቦጫረቁ የጭቃ ጅራፋቸውን ማጮህ ጀመሩ፡፡ በዚያው ዓመት በግንቦት ወር ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤታቸው ሙልጭ አድርጎ በመካድ ለመጀመሪያ ጊዜ አንድም ጋት የሚሆን የኢትዮጵያን መሬት ለሱዳን አሳልፎ ለመስጠት የተደረገ ሰምምነት የለም የሚል መግለጫ ሰጠ፡፡ ያ መግለጫ በውጭ የሚገኙትን “የዜና አውታሮች” እና “ኃላፊነት የማይሰማቸው” በበሬ ወለደ የፈጠራ ወሬ የተሰማሩ ሽብር እና ፍርሀትን በህብረተሰቡ ዘንድ የሚነዙ አሸባሪዎች ናቸው በማለት ከሷቸው ነበር፡፡ የሱዳን ባለስልጣኖች ግን ያንን መግለጫ በሚጻረር መልኩ “ከኢትዮጵያ መሬት እንዳገኙ“ በይፋ በአደባባይ ተናግረዋል፡፡ በግንቦት አጋማሽ አቶ መለስ እና አጫፋሪዎቻቸው የመሬት ማደሉን ሚስጥር ደብቀው ማቆየት ባለመቻላቸው ወደ ቀድሞው ታሪካቸው ለመመለስ ተገደዋል፡፡ በድንበር ማካለሉ ወቅት አንዳንድ የቅድመ ስራ እንቅስቃሴዎች ብቻ እንደተከናወኑ፣ እናም የተጠናቀቀ ነገር የለም በማለት በግልጽ ተናግረዋል፡፡ በቀናት ጊዜ ውስጥ አቶ መለስ እና አጫፋሪዎቻቸው ሌላ አዲስ ቅጥፈትን ፈብርከው ብቅ አሉ፡፡ የሆነው “ቀደም ሲል በንጉሱ እና በደርግ ዘመን ከሱዳን ጋር የተደረጉ ስምምነቶችን ተግባራዊ አደረግን” ብለው ጭራ ቀረሽ ዉሸት ፈጠሩ፡፡

የኢትዮ ሱዳን የድንበር ጉዳይ ኮሚቴ ጉዳዩን በግልጽ ሲያቀርበው እና በተጨባጭ በድንበሩ ባሉ አካባቢዎች ላይ ምን እየተደረገ እንዳለ ይፋ ሲያደርግ እስከ አፍ ጢሙ ተቀብትቶ/ሞልቶ የነበረው የውሸት ጎተራ መፈረካከስ ጀመረ፡፡ በአቶ መለስ ለሱዳን መሬት ዕደላ ፖሊሲ ምክንያት የተጎዱ ዜጎቻችን ለአሜሪካ ድምጽ  የአማርኛው አገልግሎት እና ለሌሎች ዓለም አቀፍ ብዙሃን መገናኛ ተቋማት ቃለመጠይቅ መስጠት ጀመሩ፡፡ በመሬት ዕደላው ምክንያት ቀጥተኛ ተጎጅ የሆኑ ወገኖቻችን አያት ቅደመ አያቶቻቸው ጠብቀው ያቆዩት መሬት በሱዳን ኃይሎች እየተወረረ ይዞታቸው ሲወሰድባቸው እና ከቀያቸው እና እትብቶቻቸው ከተቀበሩባቸው ቦታዎች ሲባረሩ የነበረውን ሁኔታ በመረረ አኳኋን የተሰማቸውን ቅሬታ በሰፊው ማሰማት ጀመሩ፡፡ የእርሻ መሳሪያዎቻቸው እና የመገልገያ ቁሳቁሶች በሱዳን ወራሪ ኃይሎች መወረሱን ገለፁ:: እንዲሁም በርካታ ኢትዮጵያውያን በሱዳን እስር ቤቶችም ታስረው እንዲማቅቁ አስታወቁ፡፡ በዚያን ጊዜ አቶ መለስ ምንም ምርጫ አልነበራቸውም፣ በግዴታ ሳይወዱ መሬት ለመስጠት ከሱዳን ጋር መፈራረማቸውን  ለማመን ተገደዋል፡፡

እ.ኤ.አ በሜይ 2008 አቶ መለስ ከኦማር አልባሽር ጋር ያደረጉትን ስምምነት እንዲህ በማለት ይፋ አድርገዋል፣ “እኛ ኢትዮጵያውያን እና የሱዳን መንግስት የድንበር ማካለሉ ስራ በሚሰራበት ወቅት ከሁሉቱም ወገን አንድም ዜጋ እንዳይፈናቀል ለማድረግ ስምምነት ተፈራርመናል… በ1996 የወሰድነውን መሬት መልሰን ለሱዳን ሰጥተናል፣ ይህ መሬት ከ1996 ዓ.ም በፊት የሱዳን ገበሬዎች ይዞታ ነበር፡፡ አንዳንድ የብዙሃን መገናኛ ተቋማት እንደሚያናፍሱት ሳይሆን በድንበሩ ዙሪያ አካባቢ አንድም የተፈናቀለ ዜጋ የለም፡፡”

እ.ኤ.አ በ2008 በዊክሊስ (የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ አመራር ሚስጥር ሰነድ) ሌላ ወሳኝ የሆኑ መረጃዎች ይፋ ተደርገዋል፡፡ “የቀድሞው የህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ማዕከለዊ ኮሚቴ አባል እና የቀድሞው የመከላከያ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ስዬ አብርሃ እንዲህ በማለት ተናግረዋል፣ ‘አቶ መለስ በኢትዮጵያ እና በሱዳን መካከል ተፈጥሮ የነበረውን የድንበር ውዝግብ ውጥረት ለማርገብ ጥረት በሚያደርጉበት ወቅት “ለአማራ ክልል ትልቅ ዋጋ ሊያስከፍል የሚችል ግዙፍ መሬት“ አቶ መለስ ለሱዳን ሰጥተዋል፡፡ እናም የአቶ መለስ አገዛዝ “በድብቅ ይዞ ለማቆየት ሞክሯል” አሉ አቶ ስዬ አብርሃ::

ቀደም ሲል አቶ መለስ፣ አሁን ደግሞ የዕኩይ ምግባር ውርስ አጫፋሪዎቻቸው ያንን ስምምነት “በድብቅ ይዘው ለማቆየት” በመውተርተር እና በመዳከር ላይ ይገኛሉ፡፡ ሆኖም ግን እ.ኤ.አ በ2008 አቶ መለስ ከኦማር አልባሽር ጋር ባደረጉት ስምምነት ላይ የሰጡት መግለጫ አንዳንድ ጠቃሚ ምልክቶችን ይሰጣል፡፡ እራሳቸው አቶ መለስ ባመኑት እ.ኤ.አ በግንቦት 2008 በእርሳቸው እና በኦማር አልባሽር መካከል በተደረገው “የመሬት መስጠት ስምምነት” ዝርዝር የስምምነቱን ሁኔታ የሚያመላክት መሆኑ የሚያጣያይቅ አይደለም፡፡ “የስምምነቱን” ሁኔታ ስናጠናው አቶ መለስ በስምምነት መዝገቡ ላይ በርካታ ጠቃሚ ማስረጃዎችን አስቀምጠዋል፡፡ “ስምምነቱ” 1ኛ) መሬቱ በሚሰጥባቸው አካባቢዎች ሰዎችን ሊያፈናቅል የሚችል ጥያቄ መነሳት እንደሌለበት 2ኛ) ከድንበር ማካለሉ ጉዳይ ጋር በተያያዘ መልኩ ከማካለል ስራው ጋር ተያይዞ ጉዳት የሚደርስባቸውን ሰዎች ጥቅሞች የማስጠበቅ ሁኔታ መኖር እንዳለበት 3ኛ) በኢትጵያውያን ገበሬዎች በህገወጥነት መልክ ተይዞ የነበረ የተባለውን መሬት ለሱዳን ገበሬዎች የባለቤትነት መብትን ማስጠበቅ 4ኛ) በ1996 ዓ.ም በህገወጥ መልክ በኢትዮጵያውያን ተይዞ የነበረውን መሬት ለሱዳናውያን መመለስ የሚሉት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡

በአቶ መለስ ፈቃድ እና አዛዥነት በእራሳቸው እና በኦማር አልባሽር የተፈረመው መሬት የመስጠት ስምምነት “የ1902 የግዌን መስመር/Gwen Line of 1902” (የ1902 የአንግሊዝ-ኢትዮጵያ ስምምነት)  እየተባለ የሚጠራው “በኢትዮጵያ እና በሱዳን መካከል ያለውን ድንበር” መስመር ማስያዝ ከሚለው ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት እንደሌለው መገንዘብ ሊሰመርበት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ እንደዚሁም እ.ኤ.አ ከ1974 በፊት በንጉሱ ዘመን እና በደርግ ዘመን ከ1995 እስከ 1991 ድረስ የተረቀቁ እና የተፈረሙ የድንበር መካለል ወይም ደግሞ መፍትሄ መስጠት ስምምነቶች ካሉ ከዚህ ስምምነት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የላቸውም፡፡ እ.ኤ.አ ከ1996 መጀመሪያ አካባቢ ጀምሮ አቶ መለስ በእራሳቸው ፈቃድ ከድንበር እና ተመሳሳይ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ መልኩ ያደረጉት “ስምምነት” በአቶ መለስ ግላዊ አተያይ የሱዳን መሬት በኢትዮጵያውያን በኃይል የተቀማ ነው በማለት በግላቸው ያደረጉት ህገወጥ እርምጃ እንጅ ሌላ ምንም ዓይነት ማስረጃ የሌለው እርባናቢሰ ስብከት መሆኑ በውል ሊጤን ይገባል፡፡

የኢትዮጵያን “ግዙፍ መሬቶች” በድብቅ እና ለህዝብ ይፋ ሳያደርጉ በሚስጥር ለሱዳን የሚሰጡበት “ስምምነት” ምክንያቱምንድን ነው”?

አቶ መለስ እና አቶ ኃይለማርያም በአጠቃላይ “በድንበር ስምምነቱ” ዙሪያ እያቀረቡት የነበረው እና ያለው የውሸት ፍብረካ ድሪቶ ሪፖርት እውነታውን ለመደበቅ ከሚሽመደመደው ድሁር አስተሳሰባቸው ያለፈ ፋይዳ አይኖረዎም፡፡ እውነተኛው የድንበር መስጠት ስምምነት እ.ኤ.አ በ2008 ተጠናቁአል፡፡ በምንም ዓይነት መልኩ ቢሆን አቶ መለስ “ግዙፍ የሆነ መሬት ከአማራ ክልል” ቆርሰው ፈርመው፣ አትመው እና አሽገው ለሱዳን መስጠታቸውና በድብቅ “በድብቅ ተይዞ እንዲቆይ” መጣራቸው የሚያጠያየቅ ጉዳይ አይደለም፡፡ እ.ኤ.አ በ2014 የኢትዮጵያ የይስሙላው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የአቶ መለስን የበከተ ውሸት እንደተለመደው “በሀሰት መጋረጃ ደብቀው” ለዘላለም ለማቆየት በማሰብ ሌላ ዘርዘር ያለ ፖለቲካዊ ድራማ ለመተወን በመውተርተር ላይ ይገኛሉ፡፡

አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ እና ጌቶቻቸው የኢትዮጵያን ህዝብ ሊያታልሉ፣ ሊያጭበረብሩ እና በውሸት ሊደልሉ የሚችሉ ይመስላቸዋል፡፡ እነዚህ የዕኩይ ምግባር ባለቤቶች መሬትን ያህል ነገር በድብቅ ሸፍኖ የመስጠት ጨዋታቸውን ኢትዮጵያውያን የማያውቁ እና የማይገነዘቡ ሞኞች አድርገው ይቆጥራሉ፡፡ እነርሱ ይህን የሞኝነት ጨዋታቸውን እንደፈለጉ መጫወት  ይችላሉ፣ ሆኖም ግን አቶ ኃይለማርያም አንድ ጥያቄ እንዲመልሱልኝ እፈልጋለሁ፣ ይኸውም “ ‘ከአማራ ክልል ግዙፍ መሬቶችን ቆርሰው የሰጡት’ “ድብቅ የሚስጥር ስምምነቶችን የት እንዳስቀመጧቸው ሊያሳዩኝ ይችላሉን? አቶ መለስ እ.ኤ.አ በ2008 እና አሁን ደግሞ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ እና የዕኩይ ምግባር አጋሮችዎ የድብቅ ስምምነቶችን ከህዝብ ፊት ደብቃችሁ ከፊታችሁ ላይ የውሸት መጋረጃ በማድረግ ለመዝለቅ የምትፈልጉት ለምንድን ነው?” ከአገር መሬት ቆርሳችሁ ለባዕድ አገር ስትሰጡ በአገሪቱ ህገመንግስት ስልጣን ለተሰጠው ፓርላማ (ለተወካዮች ምክር ቤት) ተብዬው ለይስሙላ እንኳን ቢሆን መቅረብ የለበትምን“? ህገመንግስቱ የሚለው ሌላ የስርዓቱ ቁንጮዎች የሚያደርጉት ሌላ! አራምባ እና ቆቦ!

ከላይ ለቀረቡት ጥያቄዎች መልሱ ቀላል ነው፣ እ.ኤ.አ 2008 አቶ መለስ የተናገሩለት “የሚስጥር ስምምነት“ እና አሁን ደግሞ አቶ ኃይለማርያም እያነበነቡት እንዳለው አይደለም እውነታው፡፡ ህዝብ ግብር እየከፈለ በሚያስተዳድራቸው መገናኛ ብዙሀን ብቅ እያሉ በእብሪት የሚያሰራጩት ነጭ ውሸት ነው፡፡ በእርግጥ አቶ መለስ ይዋሻሉ ማለት “መለስ ወይስ መቀልበስ” መጠሪያ ስማቸው ነው፡፡ ሁሉም አፍጥጠዉ ይዋሻሉ፡፡ አቶ መለስ እና አቶ ኃይለማርያም ከኦማር አልባሽር ጋር በስምምነቶች ላይ ያስቀመጧቸው ቃላት፣ ሀረጎች እና ዓረፍተ ነገሮች ወደ እውነት ተግባርነት የሚሸጋገሩ ከሆነ ከዚህ ጋር ተያይዘው የሚመጡ አደጋዎች ምን ሊሆኑ ይችላሉ? በእውነት እነዚህ የኢትዮጵያን ሉዓላዊ የግዛት አንድነት በመዳፈር መሬቱን እየቆረሱ ለመስጠት ተፅፈው ተፈረመው የተደበቁ ስምምነቶች የአቶ መለስን እና የአቶ ኃይለማርያምን ቀጣፊነት የሚያስረዱ መረጃዎች ሊሆኑ አይችሉምን?

ድብቅነት በኢትዮጵያ በመግዛት ላይ ላለው ገዥው አካል ዋና መለያ ባህሪው ነው፡፡ ነገሮችን ደብቆ በመያዝ እያንዳንዱን በማሞኘት ላይ ይገኛሉ፡፡ አቶ መለስ በህይወት በነበሩበት ጊዜ እና በአሁኑ ጊዜ ያሉት ሎሌዎቻቸው ደግሞ የቅብብሎሽ ዱላውን ከጌታቸው ራዕይ በመቀበል በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ እያሳዩ ያሉት ንቀት የህዝቡን ምንነት ሳይገመግሙ እና ሳይረዱ በራቁት ገላው ላይ ሱፍ እየጎተቱ መሆኑን በውል ሊያጤኑት ይገባል፡፡ አቶ መለስ እና ጋሻጃግሬዎቻቸው አሰብን እና ባድመን በቤሣ ቁርጥራጮች ካስረከቡ በኋላ ዝምታ ብቻ መልስ ስላገኙ ከዚያ ነገር አንድ ቁም ነገር ተምረዋል፡፡ ይኸውም ኢትዮጵያውያንን እና የኢትዮጵያን ግዛት የእነርሱ የግል እንደፈለጉ የሚለውጧት፣ የሚሸጧት የህግ ተጠያቂነት የሌለበት የግል ንብረታቸው መሆኗን አረጋገጡ፡፡

በመለስ/ኃይለማርያም ከምዕራብ ኢትዮጵያ የግዛት አንድነት መሬት በመቁረስ ለሱዳን ለመስጠት የሚደረግ ማንኛውም “ስምምነት” ህገመንግስታዊ አይደለም፡፡

እ.ኤ.አ. ወደ 2008 መለስ ብለን ስናይ አቶ መለስ የኢትዮጵያን መሬት ቆርሰው ለሱዳን ወይም ደግሞ ለማንም ቢሆን ለመስጠት ህጋዊ ስልጣን የላቸውም ብዬ ተከራክሬ ነበር፡፡ ዛሬም ቢሆን አቶ ኃይለማርያም የኢትዮጵያን መሬት ቆርሰው ለሱዳን የመስጠት ህጋዊ መብትም ሆነ ስልጣን የላቸውም፡፡ ይህንን ካልኩ ዘንድ አቶ መለስ “ከአማራ ክልል ግዙፍ የሆነ መሬት” ቆርሰው ለሱዳን ለመስጠት “ስምምነት” እንደተፈራረሙ አጠያያቂ ነገር አይደለም፡፡ አቶ ኃይለማርያም እና ጌቶቻቸው ይህን ህገወጥ የመሬት ዕደላ ዕኩይ ተግባራቸውን “የስልታዊ/ስትራቴጂክ ስምምነት ማዕቀፍ” በማለት የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ በመክፈት ጣፋጭ በማስመሰል በማር የተለወሰ መርዛቸውን ሊግቱን ይፈልጋሉ፡፡ እውነታው ግን በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ በስልጣን ላይ ያለው ገዥ አካል ምንም ዓይነት የኢትዮጵያን መሬት ለሱዳንም ሆነ ለማንም ሌላ አገር አሳልፎ የመስጠት ህገመንግስታዊም ሆነ ዓለም አቀፋዊ መብትም ስልጣንም የለዉም፡፡

በመጀመሪያ ደረጃ ሊታይ የሚችለው ይህ የተካሄደው የድብቅ ስምምነት የኢትዮጵያን ህገመንግስት አንቀጽ 12 የሚጻረር ስለሆነ የህገመንግስት ጥያቄን ያስነሳል፡፡ አቶ መለስ በህይወት በነበሩበት ጊዜ እና እርሳቸውን ተክተው በመስራት ላይ ያሉት የአሁኖቹ ገዥዎቻችን ከኢትዮጵያ ህዝብ እና ከተወካዮች ምክር ቤት በሸፍጥ ደብቀው ከኦማር አልባሽር ጋር ያደረጉትን የሚስጥር “ስምምነት” እየተባለ የሚጠራውን ተግባራዊ ለማድረግ ይፍጨረጨራሉ፡፡ በኢትዮጵያ ህግመንግስት አንቀጽ 12 ስር (“የመንግስት የስራ ድርሻ እና ተጠያቂነት“) እንዲህ ይላል፣ “መንግስት ተጣያቂነት እና ለህዝብ ግልጽነት ባለበት ሁኔታ ስራውን ይሰራል… ማንም የህዝብ ባለስልጣን ወይም ተመራጭ በህግ የተሰጠውን ስልጣን በህግ አግባብ ካልተጠቀመ ተጠያቂ ይሆናል፡፡” አቶ መለስ እና ተኪዎቻቸው “የህዝብ ባለስልጣን” እንደመሆናቸው መጠን ግልጽነት እና ተጠያቂነት ባለበት ሁኔታ ስራቸውን ለማከናወን ህገመንግስታዊ ግዴታ አለባቸው፡፡ ለህዝብ ሳይቀርብ እና የስምምነቱ ሁኔታም በዝርዝር ምን እንደሆነ ሳይታወቅ እንዲሁም ህጋዊ ስልጣን የተሰጠው የተወካዮች ምክር ቤት ሳያጸድቀው የአገርን የግዛት አንድነት በመጣስ መሬት ቆርሶ ለሌላ አገር ለመስጠት በእራስ ፈቃድ የሚደረግ የሚስጥር ስምምነት የህገመንግስቱን አንቀጽ 12 ይጻረራል፣ ሙሉ በሙሉም ህገመንግስቱን ይደፈጥጣል፡፡

እዚህ ላይ በአቶ መለስ እና በተኳቸው የዕኩይ ምግባር ተባባሪዎቻቸው ሸፍጥ በተሞላበት ሁኔታ በስውር መሬት ለሱዳን ለመስጠት እየተደረገ ካለው ሁኔታ ጋር በተያያዘ መልኩ ቁልፍ የሆኑ የህግ ጥያቄዎች ይነሳሉ፡፡ እነዚህም፣ 1ኛ) አቶ መለስም ሆኑ አቶ ኃይለማርያም በኢትዮጵያ ስም ሆነው ቀያጅ የሆኑ “ስምምነቶችን” ወይም “ውሎችን” በግል ለመፈረም ህገመንግስታዊ ስልጣን አላቸውን? 2ኛ) በአቶ መለስም ሆነ በአቶ ኃይለማርያም ፊርማ የሚደረጉ “ስምምነቶች” ከኢትዮጵያ ህገመንግስት አኳያ ህጋዊ ጠቀሜታ ሊኖራቸው ይችላልን? 3ኛ) በአቶ መለስ እና በአቶ ኃይለማርያም የሚደረግ/ጉ ስምምነት/ቶች በቀጣይነት በኢትዮጵያ ስልጣንን በሚይዙ መንግስታት ተግባራዊ መሆን የሚችል/ሉ መሆን እና አለመሆኑ/ናቸው ከዓለም አቀፍ ህግ አንጻር እንዴት ሊታይ ይችላል? 4ኛ) በአቶ መለስ እና አቶ ኃይለማርያም በተፈረመ ስምምነት የተሰጠ የትኛውም በሱዳን የተያዘ የኢትዮጵያ ግዛት በዓለም አቀፋዊ ህግ መሰረት በሌላ አገር እንደተያዘ ሊታይ የሚችል ነው ወይስ አይደለም? 5ኛ) የኢትዮጵያ ህገመንግስት በግልጽ እንዳስቀመጠው “የፌዴራል መንግስቱ ስልጣን እና ኃላፊነቶች” መካከል “የውጭ ፖሊሲ ማውጣት እና መተግበር፣ ዓለም አቀፍ ውሎችን መዋዋል እና ማጽደቅ“ “የፌዴራል መንግስቱ” አጠቃላይ የውጭ ግንኙነቶች እና ስልጣኖች በስራ አስፈጻሚ ማኔጅመንት ተፈርመው የውጭ ግንኙነት መስኮች እና “የዓለም ዓቀፋዊ ስምምነቶች“ በፓርላማው ይጸድቃሉ/አይጸድቁም፡፡ አንቀጽ 55 (12) በግልጽ እንዳስቀመጠው ዓለም ቀፍ ስምምነቶችን በሚመለከት በስራ አስፈጻሚው ተፈርሞ ለተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ በፓርላማው ታይቶ ይጸድቃል፣ የተወካዮች ምክር ቤት ከተሰጡት ዋና ዋና ኃላፊነቶች አንዱ ስራ አስፈጻሚው ዓለም አቀፍ ስምምነቶችን ህጎችን ፈርሞ ሲያቀርብለት ፓርላማው መርምሮ ያጸድቃል፡፡”

የአቶ መለስ እና አቶ ኃይለማርያም በራሳቸው ፈቃድ መሬት ለመስጠት የሚያደርጓቸው “ስምምነቶች”  የህገመንግስቱን አንቀጽ 55 (12) የሚደፈጥጥ ነው፡፡ አቶ መለስ እና አቶ ኃይለማርያም ከሌላ መንግስታት ጋርም ስምምነቶችን ለመደራደር እና ለመፈረምም ይችላሉ፡፡ በህገ መንግስቱ የተሰጣቸው ስልጣን ለመደራደር፣ ለማርቀቅ እና ዓለም አቀፋዊ ስምምነቶችን በመፈረም ላይ ብቻ የተወሰነ ነው፡፡ ሆኖም ግን አቶ መለስ እና አቶ ኃይለማርያም ከሌላ መንግስታት ጋር የሚያደርጓቸው “ስምምነቶች” ፊርማ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአንቀጽ 55 (12) በግልጽ እንደተቀመጠው ሁሉ ካልጸደቀ በስተቀር የተጻፈበትን ወረቀት ዋጋ ያህል አያወጣም፡፡

አቶ መለስ እና አቶ ኃይለማርያም ሁለቱም መሬት ለመስጠት ከሱዳን ጋር ያደረጓቸውን ስምምነቶች ፓርላማው እንዲያጸድቃቸው ለማቅረብ ፈቃደኞች አልሆኑም፡፡ እንዲሁም በጨዋነት መንፈስ ቢያንስ ፓርላማው እንዲወያይበት እንኳ ስምምነቶች ለመስጠት ፈቃደኞች አልሆኑም፡፡ ስምምነቶችን ፓርላማው እንዲያጸድቃቸው ለማቅረብ አለመቻል ህገመንግስታዊ የስራ ኃላፊነት ድርሻን እና መርሆዎችን የጣሰ ከመሆኑም በላይ ፓርላማው ዓለም አቀፍ ስምምነቶችን ለማጽደቅ ባለው ስልጣን ላይ እየተደረገ ያለ ጣልቃገብነትን የሚያመላክት ነው፡፡

አንቀጽ 86 “የውጭ ግንኙነት መርሆዎችን“፣ የ“ፌዴራል መንግስትን“ (የጠቅላይ ሚኒስትሩን፣ የተወካዮች ምክር ቤትን) ኢትዮዮጵያ ከሌሎች አገሮች ጋር እና ከዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ጋር ያላትን ግንኙነት ይገልጻል፡፡ አንቀጽ 86 ንኡስ አንቀጽ 1 እና 3 የፌዴራል መንግስቱ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ “በእኩልነት እና በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ፣ ዓለም አቀፍ ህጎች እንዲከበሩ የማድረግ፣ የኢትዮጵያን ህዝብ ጥቅም ማስጠበቅ“ እና ዓለም አቀፍ ህጎች እና ስምምነቶች እንዲከበሩ፣ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት እና ከህዝብ ፍላጎት በተጻራሪ የሚቆሙትን እንደማይቀበል በግልጽ ያስቀምጣል፡፡

አቶ መለስ እና አቶ ኃይለማርያም ከሱዳን ጋር የተፈረመውን ስምምነት ሚስጥር አድርገው የያዙበት ዋናው ምክንያት እነዚህ ስምምነቶች የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት በግልጽ በአገጠጠ እና በአፈጠጠ መልኩ የሚጥሱ መሆናቸውን ስለሚያውቁ ዕኩይ ምግባሮቻቸውን ለመደበቅ ያሰቡት የሸፍጥ ስራ ነው፡፡ እነዚህ የሸፍጥ ሰዎች “ስምምነቶችን” ሚስጥር ማድረግ ይፈልጋሉ ምክንያቱም የኢትዮጵያን ጥቅም አሽቀንጥረው የጣሉ በመሆኑ እውነታው በተጫባጭ ጎልቶ እንደሚታይ እና ከኢትዮጵያ ጥቅም በተቃራኒ የቆሙ ከሀዲዎች መሆናቸውን ያውቃሉ እና ነው፡፡ ስምምነቱን ሚስጥር አድርጎ መያዝ ከላይ ከተጠቀሱት የተለዬ ሌላ ምክንያት በፍጹም ሊኖር አይችልም፡፡ በሌላ በኩል ሚስጥር አድርገው የያዟቸውን ስምምነቶች ግልጽ ያድርጉ እና እኔ እነዚህ ስምምነቶች የተደረጉት እኩልነትን ባዛነፈ መልኩ ነው፣ ኢትዮጵያን ብቸኛ ተጎጅ ያደረገ ነው እያልኩ የምሟገተውን በመርታት ማስተባበል ይችላሉ፡፡

አንቀጽ 9 (“የህጎች ሁሉ የበላይ“) ይህንን አስመልክቶ ህገመንግስቱ የአገሪቱ የህጎች ሁሉ የበላይ መሆኑን በግልጽ ያስቀምጣል፡፡ ሁሉም ህጎች፣ ወጎች፣ ልማዶች እና በመንግስት አካላት የሚደረጉ ውሳኔዎች ወይም የህዝብ ባለስልጣኖች ከዚህ ጋር በተያያዘ መልኩ ተጻራሪ ሆነው ከተገኙ ተፈጻሚነት አይኖራቸውም፡፡ ሁሉም ዜጎች፣ የመንግስት አካላት፣ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ ሌሎች ማህበራት እና ባለስልጣኖቻቸው ህገመንግስቱን ማክበር ማስከበር እና በህጎቹም መገዛት… ማንኛውም ስልጣንን ለመያዝ የሚፈልግ አካል ሁሉ በህገመንግስቱ ከተደነገገው ውጭ ስልጣንን ለመያዝ ማሰብ የተከለከለ መሆኑን በግልጽ ያመላክታል፡፡”

በአቶ መለስ እና አቶ ኃይለማርያም የሚደረግ ማናቸውም “ስምምነት” “ውል” “የጋራ ስምምነት” “ድርድር” አንቀጽ 55 (12)፣ አንቀጽ 86 (2) (3) ተፈጻሚነት አይኖረውም፡፡ በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ህገመንግስት ተፈጻሚነት የማይኖረው ህግ ወደፊት ስልጣን የሚይዙ ህጋዊነትን የተላበሱ ተከታታይ የኢትዮጵያ መንግስታት ሊቀበሉት የማይችል ዓለም አቀፍ ህግ በኢትዮጵያ ተፈጻሚነት ሊኖረው ይችላልን?

አንቀጽ 9 (4) የኢትዮጵያ ህገመንግስት እንዲህ ይላል፣ “በተወካዮች ምክር ቤት የጸደቁ ዓለም አቀፍ ስምምነቶች“ የአገሪቱ የህጎች ሁሉ የበላይ ናቸው፡፡” ሌሎችስ በኢትዮጰያ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያልጸደቁ ዓለም አቀፍ ህጎች ምን ሊባሉ ነው?  ይህንን ጥያቄ ለመመለስ ማንም ቢሆን የህገመንግስት ልሂቅ መሆንን አይጠይቅም፣ ዓለም አቀፍ ህጎች በኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እስካልጸደቁ ድረስ የተጻፉበትን ወረቀት ያህል ዋጋ አያወጡም፡፡ ማንም ህጋዊነትን ተላብሶ ስልጣን የሚይዝ ቀጣይ የኢትዮጵያ መንግስት ተፈጸሚነት በማይኖራቸው ህጎች ዓለም አቀፍ ስምምነቶችን የመፈጸም ግዴታ የለበትም፡፡ ኢትዮጵያ እንደዚህ ያሉትን ስምምነቶች የማውገዝ እና ሱዳኖች ከህግ አግባብ ውጭ በተጽዕኖ ከያዟቸው ይዞታዎች ለኢትዮጵያ አስረክበው በዓለም የህግ አግባብ መሰረት ከኢትዮጵያ ግዛት እንዲወጡ ይደረጋል፡፡

የዓለም አቀፋዊው ህግ ስምምነቶች በመንግስታት መካከል መተግበር እንዳለባቸው ግዴታ የሚጥል እንደመሆኑ መጠን (ስምምነቶች መጠበቅ አለባቸው በሚለው መርሆ መሰረት) እንደዚሁም የተወሰኑ የህግ ማዕቀፎች መንግስት ሊያወግዛቸው እና ከመተግበርም ሊቆጠብ የሚችልባቸው (ሊያቋርጣቸው) ወይም ደግሞ በመጀመሪያ ስምምነቶቹ በሚፈረሙበት ጊዜ ስህተት ተሰርቷል ብሎ ካመነ እና ካረጋገጠ ስምምነቶችን ሊሰርዛቸው ወይም ከስምምነቶች እራሱን ሊያገል እንደሚችል ዕድል ይሰጣል፡፡

የቬና ስምምነት በህግ ውል ላይ ውዝግብ በሚነሳበት ጊዜ ውሳኔ ሊያሳልፍ እንደሚችል ብዙ ስምምነቶች የህግ መሰረት የሌላቸው ብሎ ውድቅ ሊያደርግ እንደሚችል በግልጽ ያስቀምጣል፡፡ አንቀጽ 46 (1)፣ (2) (“ተፈጻሚነት የማይኖራቸው ውሎች“) ተፈጻሚነት የማይኖራቸውን ስምምነቶች ከአንድ አገር “የውስጥ ህጎች” አንጻር ተፈጻሚነት ሊኖራቸው እንደማይችል ከግንዛቤ በማስገባት እንዲህ ይላል፣መንግስት ለአንድ ስምምነት ተገዥ ሊሆን የሚችለው በሀገሩ ያለውን ህግ የሚጥስ እስካልሆነ ድረስ እና ያደረገው ስምምነትም በአገሪቱ ካለው የህግ ማዕቀፍ ጋር የማይቃረን እስከሆነ ድረስ ብቻ ነው፡፡በተግባር እና በልማድ መተግበር ካለበት ሁኔታ ውጭ በሆነ መልኩ አንድ መንግስት በእራሱ ህግ አውጥቶ ስምምነት ቢገባ ተፈጻሚነት ሊኖረው አይችልም፡፡

አንቀጽ 49 የሚከተለውን መብት ያጎናጽፋል፣ “አንድ መንግስት ከሌላ እምነት ከማይጣልበት መንግስት ጋር ስምምነት ቢዋዋል ይህ ውል ተፈጻሚነት አይኖረውም“ አንቀጽ 50 እንዲህ ይላል፣ “መንግስት ከሌላ መንግስት ጋር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ የማይገባ ጥቅም በመስጠት ውል የተዋዋለ ከሆነ ያ ውል በአገሪቱ ህግ ተፈጻሚነት አይኖረውም“ መንግስቱን ወይም ደግሞ የመንግስቱን ተወካይ በማስገደድ የተደረገ ስምምነት ካለ ይህ የግዳጅ ስምምነት ስምምነቱን ለማፍረስ መሰረት ይሆናል፡፡

ሊካድ የማይችለው ነገር እነዚህ ተአማኒነት የሌላቸው ስምምነቶች በአቶ መለስ እና በአቶ ኃይለማርያም በሁለቱም ባለስልጣኖች የተፈረሙ ቢሆንም ከላይ በግልጽ ለማመልከት እንደተሞከረው ከኢትዮጵያ ህገመንግስት አንጻር ተፈጻሚነት አይኖራቸውም፡፡ ሌሎች ሊነሱ የሚችሉ ጥያቄዎች ቢኖሩ የሚከተሉት ናቸው፣ 1ኛ) አንቀጽ 55 (12) ከሚፈልገው የህግ ማዕቀፍ አንጻር ከሱዳን ገዥ አካል ጋር ገና ስምምነቶቹ ሲፈረሙ ግልጽ በሆነ መልክ ጉዳዩ ለሚመለከተው ፓርላማ ቀርቦ እንዲጸድቅ የተደረገ መሆን አለመሆኑ፣ 2ኛ) ስምምነቱ በሚከናወንበት ወቅት “ሙስና” እና “የማጭበርበር ወንጀል” የነበረ ወይም ያልነበረ መሆኑ፣ 3ኛ) ስምምነቱ በሚካሄድበት ጊዜ “አስገዳጅነት” ያላቸው ወይም ለማስገደድ የሚያበቁ ድርጊቶች የነበሩ ወይም ያልነበሩ መሆናቸው፣ በኢትዮጵያ ወገን በኩል ህጉን መርምሮ የማጽደቅ ሂደት ያልተከናወነ ስለነበር ኦማር አልባሽርን በሚጠቅም መልኩ የተፈጸመ እንዲሁም ስምምነቱ ለኢትዮጵያ የተወካዮች ምክር ቤት እንዲቀርብ እና እንዲጸድቅ ያልተደረገ ስለሆነ የተፈጻሚነት ዕድል እንደማይኖረው የሚያጠራጥር አይደለም፡፡ በቬና ስምምነት መሰረት ሱዳን ለኢትዮጵያ መንግስት ስምምነቱን የማጽደቅ ዕድል መስጠት እንዳለባት የህግ ግዴታ አለባት፡፡ እራሷን ከጉዳዩ ጋር በማስተሳሰር በተለመደው ልምድ እና እምነት መሰረት ሱዳን ስምምነቱን ለማጸደቅ ስራዎችን ልትሰራ ይገባል፡፡ በአጠቃላይ ከስምምነቱ ጋር በተያያዘ መልኩ ሚስጥር ሆኖ መያዙ እና በስምምነቱ ዙሪያም ምንም ዓይነት ፍንጭ እንዳይኖር ድብቅ ለማድረግ ከሚደረገው ጥረት አንጻር ወደፊት ስምምነቱን በጥልቀት እና በዝርዝር በመመርመር የሚገኘው የመረጃ ውጤት ሙስና፣ የማጭበርበር ወንጀል እና የግዳጅ ውል ሆኖ ይገኛል፡፡

የኢትዮጵያን መሬት ለሱዳን የመስጠት ስምምነቶችን ተፈጻሚነት የመሆን ዕድል የሚጻረሩ ሌሎች ህገመንግሰታዊ ጉዳዮች

አቶ መለስ እና አቶ ኃይለማርያም ግዙፍ የሆነ መሬት “ከአማራ የግዛት ክልል” በመቁረስ ለሱዳን በማስረከባቸው የአማራን ህዝብ የጋራ መብቶች ደፍጥጠዋል፡፡ “ስምምነቶቹ” አንቀጽ 39ን (የብሄር ብሄረሰቦች እና ህዝቦች መብት) እንዲሰጥ ስምምነት በተደረገበት መሬት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን በግዳጅ ከሉዓላዊ ግዛታቸው በመነጠል ከፍላጎታቸው ውጭ ወደ ሱዳን አሳልፎ የሚሰጥ ስለሆነ ህጉ ተፈጻሚነት እንዳይኖረው ይጻረራል፡፡ አቶ መለስም ሆኑ አቶ ኃይለማርያም መሬት የማስመለስ፣ ብልህነት በጎደለው መልኩ በግዛት ላይ እና በግዛቱ በሚኖሩ ህዝቦች ላይ ድርድር የማድረግ ወይም ደግሞ በእራሳቸው ውሳኔ “የብሄሮችን እና የህዝቦችን” በመሬታቸው ላይ ያላቸውን መብት በመንጠቅ ሳይጠየቁና ምክር እንዲያደርጉ ዕድል ሳያገኙ በሌላ አባባል ሪፈረንደም ሳይሰጥ የመሬት ግዛታቸውን በድብቅ በተሸፈነ ሴራ በመንጠቅ ለሌላ አገር አሳልፎ የመስጠትም ሆነ ስምምነት የማድረግ ህገመንግስታዊ ስልጣን የላቸውም፡፡ በዓለም አቀፋዊ ህግ መሰረት መንግስት የአንድን አገር ሉዓላዊ ግዛት ለሌላ ባዕድ አገር አሳልፎ ከመስጠቱ በፊት ሊሰጥ በታሰበው መሬት ላይ ወይም በዚያ ግዛት ላይ የሚኖሩ ህዝቦችን የማማከር ግዴታ አለበት፡፡ ማማከር ሲባልም የህግ ሂደቱን ለመጠበቅ እንጅ መንግስት ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ መልኩ እጁን ዘው አድርጎ በማስገባት ምንም ዓይነት ውሳኔ መስጠት እንደማይችል ልብ ሊባል ይገባል፡፡ ይህም ሆኖ “በአማራ ክልል የሚገኘውን ግዙፍ የመሬት ግዛት” ለሱዳን መንግስት አሳልፎ ለመስጠት ስምምነት ከመፈራረማቸው በፊት በአቶ መለስም ሆነ በአቶ ኃይለማርያም በኩል ህዝቡን ለማማከር የተሞከረ ነገር የለም፡፡

ከዚህም በላይ የኢትዮጵያ ህግመንግስት አንቀጽ 2 የሚከተለውን መብት ያጎናጽፋል፣ “በዓለም አቀፍ ህግ ስምምነት እና ኢትዮጵያም ተቀብላ ባጸደቀቸው ህግ መሰረት የኢትዮጵያ ሉዓላዊ የግዛት አንድነት በአገሪቱ ውስጥ የሚገኙ አባል ክልላዊ መንግስታት ፌዴሬሽን ድንበሮችን አካትቶ የያዘ ነው፡፡“ ይኸ ህገመንግስታዊ ቋንቋ የአገር ውስጥ እና የውጭ የወሰን ድንበሮቻቸው ሲካለሉ እና ሲዘጋጁ “የክልል አባል መንግስታት” የሚኖራቸውን ቀጥተኛ ሚና መስተጋብር በግልጽ ያሳያል፡፡ የህገመንግስቱ አንቀጽ 2 የኢትዮጵያ የፌዴራላዊ መንግስት አካል መሬቱን ለሱዳን አሳልፎ የሚሰጠውን ስምምነት ከመፈረሙ በፊት “በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት” የወሰን ክልል ውስጥ የሚኖረው ህዝብ ሪፍረንደም/referendum (ጠቅላላ የህዝብ ድምጽ) ማድረግ እንዳለበት በግልጽ አስቀምጦታል፡፡

ከሱዳን ጋር የተደረገው ህገወጥ ስምምነት ተፈጸሚነት ስለማይኖረው ብዙም አያሳስብም

በአቶ መለስ፣ አቶ ኃይለማርያም እና ጓዶቻቸው የተደረገው ህገወጥ ስምምነት ተፈጻሚነት የማይኖረው ቢሆንም በመጠኑም ቢሆን አሳስቦኛል፣ ሆኖም ግን በግልጽ እና ጥልቀት ባለው መንገድ ሳገናዝበው ብዙ የሚያሳስበኝ አይሆንም፡፡ “ስምምነት” እየተባለ ስለሚጠራው ጉዳይ ብዙ የሚታወቁ ድብቆች አሉ፡፡ ስምምነቶቹን ካባ ደርበው ትልቅ ነገርን እንደፈረሙ እናውቃለን፡፡ ሆኖም ግን ምን እንደደበቁ በእርግጠኝነት ለመናገር አይቻልም፡፡ ስምምነቶቹን ከህግ አግባብ ውጭ በሙስና እንዳደረጉ እናውቃለን፣ ሆኖም ግን የሙስናውን ስፋት እና ጥልቀት እስከምን ድረስ እንደሆነ በግልጽ አይታወቅም፡፡ ስምምነቶቹ ሲፈጸሙ ማታለል እንዳለባቸው እናውቃለን፣ ሆንም ግን የማታለሉ ደረጃ እስከምን ደረጃ እንደሆነ አናውቅም፡፡ ስምምነቶቹ ሲፈጸሙ ማጭበርበር እንዳለባቸው እናውቃለን፣ ሆኖም ግን የማጭበርበሩ ስፋት እና ጥልቀት ደረጃ እስከምን ድረስ እንደሆነ አናውቅም፡፡ የስምምነት ሰነዶች ሲፈረሙ ሁሉንም ዓይነት ያካተቱ ማጭበርበሮች እንዳሉ እናውቃለን፣ ሆኖም ግን የማታለል፣ የማጭበርበር እና የመሰሪነት ዓይነቶችን አናውቅም፡፡ በድብቅ የተፈረሙት ስምምነቶች እና አሁንም ሚስጥር ሆነው የተያዙት ድሁር እና ኮሳሳ ስምምነቶች ወደፊት በጊዜ ሂደት እርቃናቸውን ወጥተው ሚስጥሩ ግልጽ የሚሆንበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ”እውነት ለዘላለም ተቀብራ እንደማትኖር ሁሉ ተንኮልም በዙፋን ላይ ለዘላለም ተቀምጣ አትኖርም”፡፡

የኢትዮጵያ የግዛት ሉዓላዊነት አንድነት በምንም ዓይነት መልኩ ለድርድር አይቀርብም፡፡ አቶ መለስ ዜናዊ፣ አቶ ኃይለማርያም ዳሳለኝ…ሌላም ማንም… ቢሆን በኢንቨስትመንት የማስመሰያ ጨዋታ የኢትየጵያን ለም መሬቶች በቅርጫ ለሱዳን፣ ለሳውዲ ወይም ለህንድ “ባለሀብቶች” ሊሰጥ አይችልም፡፡ እውነታው ግን ጀሴ ጀምስ እና ወሮበላ ጓዶቹ (በአሜሪካ የታውቁ ዘራፊዎች) የዘረፏቸውን ባንኮች ለሌላ የመስጠት መብት እንዳላቸው አድርገው እንዳሰቡት ሁሉ የኢትዮጵያ ቁንጮ አምባገነን መሪዎች ደግሞ የኢትዮጵያን ለም መሬት የመስጠት መብት እንዳላቸው ቆጥረውታል፡፡

ጥንታዊ የሆነች ኢትዮጵያ የምትባል አገር አለች፣ የእኛ እናት ሀገር፡፡ ኢትዮጵያ በክልል መከፋፈል የለባትም፣ “በጎሳ ፌዴራሊዝም” መበጣጠስ የለባትም፣ ወይም ደግሞ በድንበር መካለል ሰበብ “ስምምነት” መሰረት ግዛቷ መሸጥ የለበትም፡፡ ወደ የግዛት ሉዓላዊነት አንድነቷ የተጠበቀች ኢትዮጵያ ስንመጣ ኦሮሞ ኢትዮጵያ የለችም፣ አማራ ኢትዮጵያ የለችም፣ ትግሬ ኢትዮጵያ የለችም፣ ጉራጌ ኢትዮጵያ የለችም… ወይም ደግሞ ጋምቤላ ኢትዮጵያ የለችም፡፡ በቀላሉ አነጋገር የኢትዮጵያ ህዘቦች ኢትዮጵያ ናት ያለችው፡፡ በሉዓላዊነት የግዛት አንድነት ዙሪያ በመሰባሰብ ኢትዮጵያ የማትከፈል እና የማትከፋፈል መሆኗን በማመን መተባበር አለብን፡፡ ምንጊዜም ቢሆን ጠንቃቃ ሆነን መገኘት አለብን፣ እናም ከመቃብር አፋፍ ላይ ሆነው ለማትረፍ የሚፈልጉ ተንኮለኛ ጭራቆችን እራሳቸው በመቃብር ውስጥ እንዲቀሩ እናድርግ፡፡ አምላክ ሁላችንንም አንድ አድርጎ እንደፈጠረን ሁሉ በፍቅር እና በመከባበር በአንድነት በመኖር ለአምባገነንነት፣ ለጨፍጫፊነት፣ ለመለያየት ቦታ መስጠት የለብንም፡፡ ዛሬም አንዲት ኢትዮጵያ! ነገም አንዲት ኢትዮጵያ! ለዘላለምም አንዲት ኢትዮጵያ!

 ኢትዮጵያ  ለዘላለም  በክብር  ትኑር!

 ጥር 27 ቀን 2006 ዓ.

 EMF

posted by Tseday Getachew

ወጣቶች ኩርፊያ-በኢትዮጵያ!

ethiowaga.gif
(ጥራኝ ጎዳናው! ጥራኝ መንገዱ!)

የኢትዮጵያ ወጣቶች በሦስት መስቀለኛ መንገዶች ላይ ቆመዋል፡፡ የመጀመሪያው መንገድ ከባህልና ከልማድ የተወረሰ ነው፡፡ ዘፈን፣ ቀረርቶና ሽለላም አለው፡፡ አፋሩ፣“ዳሀር ቦር ናሬ!” ይላል፡፡ (“ግመሎቼና ከብቶቼ፣ እውጪ ማደር ልማዳችሁ ነው፤ እኔም እንደናንተ ጠላቴን ሳመነዥገው ደጅ-አድራለሁ!” እያለ ይዘፍናል፡፡) ኦሮሞውም፣“አቢቹ ነጊያ ነጊያ!” የሚል ዜማ አለው፡፡ (የወንድሞችህን ገዳዮች አሰቃይተህ እስከምትገላቸው ድረስ፣ እንቅፋትም አይንካህ! ድል-በድል ያድርግህም!” የሚል መልዕክት አለው፡፡ የአማርኛ ተናጋሪውም ቢሆን፣ “ጥራኝ ደኑ! ጥራኝ ዱሩ!….ላንተም ይሻልሃል ብቻ ከማደሩ!” እያለ ይሸልላል፡፡ ይህ የሚሆነው እንግዲህ ወጣቱ ያኮረፈ ጊዜ ነው፡፡ ምክንያቱ ሊለያይ ይችላል፤ ነገር ግን፣ ወጣቱ ኩርፊያውን ለመግለጽ የሚጠቀምበት ባህላዊ መንገድ “ሽፍትነትን” ነበር፡፡ Read full story from semnaworeq

EMF

posted by Tseday Getachew

Post Navigation