Fitih le Ethiopia

I wish democracy and unity for Ethiopia

Archive for the month “March, 2014”

ሃገራዊ ጥሪ ከ 2007 ምርጫ በፊት!

ስለ ሃገራችን ኢትዪጵያ መከራ፣ ስለ ህዝባችን ስቃይ፣ ስለ ኢህኣዴግ ግፍ፣ ስለ ተቃዋሚዎች ህብረት ኣልባ መሆን፣ ሌላም ሌላም ከሚገባው በላይ ተጽፈዋል፣ ተነግረዋል፣ ነገር ግን ያመጣነው ለውጥ የለም – እንዲያውም የባሰ መለያየት፣ መወቃቀስ፣ ማጥላላት፣ እና የኢህኣዴግን ኪስ እንዲሰፋ ኣስተዋጽኦ ኣድርገናል። ኣሁንም ኣሁንም ለውጥ ከተፈለገ እኛ ራሳችን መለውጥ ኣለብን: የሃገር ሃገራዊ ራእይ ኣግኝተን መስማማት የግድ ይላል።

ኣሉታዊ ኣስተዋጽኦ
በብልጣብልጥ እና በኣጭር ጊዜ ስልጣን ለመጨበጥ የሚደረገው ሩጫ ካለፈው 20 ኣመት እንዳየነው የትም ኣያደርስም። ለስልጣን መውጣጫ የሚደረጉ ኣስመሳይ ፈጠራዎች ሁሉም ነቅቶባቸዋል፣ ሰዎች ዝም ይበሉ እንጂ በልባችው መሳቃቸው ኣልቀረም። በዘር፣ በጎሳ፣ በጥቅማጥቅም ወዘተ የሚደረጉ ስብስቦችና መሳጥሮች ስንቶችት በታትነዋል:: በኣንጻሩ ደግሞ ኢሕኣዴግን ከነበረው ደካማነት ኣጠናክረውታል።

ስለዚ መጠላለፉ እና ሩጫው ይቅርና ረጋ ብለን ተሰባስበን፣ ተነጋግረን፣ ተመካክረን፣ ላይ ታች ብለን፣ ግዝያዊ የሃገር ኣመራር መመስረት የግድ ይላል። ወደ ሌላ ውጥን ሳንሄድ በቅድሚያ ያሉትን ድርጅቶች ተሰባስበው ግዝያዊ የሽግግር መድረክ እና ስርኣት – መመስረት ኣለባቸው። ከፓሪስ ኮንፈረንስ፣ ከኢድሃቅ ፣ ከህብረት፣ ከቅንጅት….መማር መቻል ኣለብን።

ስላለው የድሮ ታሪካችን ብቻ እያወራን እኛ ግድፈት የሞላበት ታሪክ እየሰራን መሆናችን ማወቅ ኣቅቶናል። ኣገራችን ለመጀመርያ ግዜ ወደብ ኣልባ ሁናለች (የተጀመረው ግን ከዓድዋው ጦርነት ጣልያን መረብ ምላሽ ሲቆጣጠር ነው) ፣ ገበሬዎች ከርስታቸው እየተፈናቀሉ; መሬታቸው ለባእዳን በርካሽ ዋጋ እየተክራየ ይሰቃያሉ፣ መንግስት ህገ መንግስት ተገን ኣድርጎ የፈለገው ያስራል፡ ያሰቃያል፡ ይገድላል፡ ይበትናል ወዘተ፣ ለሱዳን መሬት እየተሸጠ ነው፣ ፍርድ ቤቶች የመንግስት ፓለቲካ መሳርያ ሁነዋል፤ ታዲያ ከዚህ ሁሉ የባሰ ምን ሊመጣብን ነው። ይህን ሁሉ ማገናዘብ ኣቅቶን ለመፍትሄ መተባበር ሰንፈን መጠላለፍ ማንነታችን ኣድርገነዋል።

ትምክህተኝነት ከዛም ጠባብነት እንዲሁም መጠላለፍ ኣሁን ደግሞ ሙስና ኣገሪትዋን እየዶቆሳት ነው። ከጅማሪዎች የነበረች ሃገር። ታሪኳና ባህልዋ እያከሰምን ወደ ታች ዓዘቅት እየከተትናት መሆናችን እና ጸጸቱ ኣብሮን እንደሚቀበር ማወቅ ኣለብን። ከዚህ ውርደት ተስማምተንና ተከባብረን በሰላም መኖር እንዴት ያቅተናል። ጣልያንን ያሸነፉ ኣያቶቻችን እኮ ወድ ህይወታችው ገብረው ነው እንጂ እንደኛ እየተለጣጠፉ ኣልነበሩም።

ሁላችን ማውቅ እና መቀበል ያለብን ኣንድ ድርጅት ብቻው ስልጣን ልይዝበት የሚችል ግዜ ኣብቅተዋል። እስካሁን ድረስ በነበሩት ኣስከፊ የከፋፍለህ ግዛ ስርዓቶች ምክንያት በህዝብ ላይ ነቀርሳ ፈጥረዋል። የይቅርታና የእርቅ ስራ ኣልተሰራም። ሰለዚህ መተማመን የለም። ሙሱናም የሰዎች ራእይ ሁነዋል:: ይህ ለመንቀል የተደራጀ ሃይልና ህግ ያስፈልጋል። ይቻላልም።

ስለዚህ ከዚህ ሁሉ ውጣ-ውረድ ተምረን በህይወታችን መልካም ስራ ሰርተን ለመኖር እንብቃ። ለራሳችን ቃል ገብተን እንነሳ። የሌሎች ተበደልን የሚሉትን ወገኖች ብሶት ለማዳመጥ ትእግስት ይኑረን። ያኔ ነው ተግባብተን ለመስራት የሚቀለን። ከሙሱና ነጻ ሁነንም ገለልተኛ የፍትህ ተቋማት እያስፋፋን ህዝባችንን እያስተባበርን እየተረዳን፣ መልካም ስራ በመስራት ራሳችንን ደስ ኣሰኝተን፣ ሃገራችንን እየረዳን፣ ለተተኪ ትውልድ ገንቢ ባህል እያስተላለፍን፣ ሌሎችም በድህነት ሳይሆን በክብር እንዲያውቁን ማድረግ የምንችለው።

ኣወንታዊ ኣስተዋጽኦ
ኣሁን ተቃዋሚ ድርጅቶችን የሚያጣላቸው ፕሮግራም ወይም ፓሊሲ መኖር ኣልነበረበትም: ከነጻ ምርጫ ስርዓት ጋር ተያይዞ ህዝቡ ሊቀበላቸው ላይችል እኮ ይችላል፣ ግዜው እንዴት እየተለዋወጠ እንዳለ ለምን ኣይረዱም; ቢሆንስ ፍጽማዊ የሆነ ፕሮግራም እኮ የለም ዋናው በሰላም መመካከር እንጂ።

1. በሃገር ውስጥ ያሉ ተቃዋሚ ድርጅቶች ተባብረው ለመስራት በንኡስ ፕሮግራምም ቢሆን መስማማት ኣለባቸው።
2. በውጭ ያሉት ተቃዋሚ ድርጅቶችም የበለጠ ሰፊ ስብስብ መፍጠር ይጠበቅባቸዋል።
3. የሃገር ውስጥና የውጭውን ደግሞ የመንግስት ተንኮል ግምት ውስጥ በማስገባት ግንኙነቱ በዚህ ኣንጻር ሊከናወን ይችላል; ዋናው መተማመን እና ላንድ ኣላማ መቆም ነው።

የተቃዋሚ ድርጅቶች፡ ኣንድነት (USA)፣ ሸንጎ፣ ግንቦት 7፣ ኦነግ፣ ኢህኣፓ፣ መኢሶን ሌሎችም ተባብራችሁ ማእከላይ ኣመራር መስርታችሁ፣ የውጭውን ግፊት መምራት እና በሃገር ውስጥ ላሉት ተቃዋሚዎች የሚገባውን ድጋፍ እና ኣጋር መሆን ነው። ሌላ ኣማራጭ ኣለን የሚል ካለ መልካም። ከኢሳያስ ኣፈወርቂ በኩል የሚደረግ ስልታዊ ትብብር ግን ከጠቀሜታው ጉዳቱ ከመጠን ያለፈ እንደሆነ ያለፍት 40 ኣመታት ተመኩሮ ኣስተምሮናል። የጋራ ማእከላይ ኣመራሩ ከተቀበለው ግን ልንስማማበት እንችላለን።

ልዩነትን ተቻችሎ ሀገር መገንባት
እስካሁን ድረስ እንደታዘብነው እርስ በርሳችን መጠላለፍ፣ ለኢህዓዴግ በጎሳና በዘር እየፈረጅን እኛው ራሳችን በጎሳና በዘር ተሰባስበናል፣ ተበደልን የሚሉት ሳናዳምጣቸው ኣልተበደላችሁም እንድያውም ደልትዋችሃል ብለናቸዋል፣ ብሄራዊ ማንነታችን ያለ ህብረት ሊጎለብት ኣይችልም; ህብረት ደግሞ ኣላከበርንም; ተከተሉን እናውቅላችሃለን በዝተዋል። ሀገር ለመገንባት ልዩነትን ኣቻችሎ መደማመጥ; መከባበር; ለበጎ ስራ መትጋት ይጠበቃል። ሁላችን መሪዎች መሆን ኣንችልም ኣንድ መሪ ግን ማስቀመጥ ኣለብን። ትእግስትና ስብእነት ያስፈልጋል።

ኢህኣዴግ መውደቁ ሲቃረብ የተኪው ህብረት ጎልብቶ መውጣን ደግሞ ኣይታይም፣ እንዲያውም ሻክረዋል። ይህ ኣይነት ሂደት የሶማልያ የኢራቅ የኣፍጋኒስታን የመሳሰሉትን ሁኔታዎች እንዲከሰት በር ከፋች ነውና። ኢህኣዴግ ቢውድቅ ምን የፈጠርነው ኣብሮ የመስራት ባህል ኣለና? ልዮነትን ኣክብሮ መሰረታዊ በሆኑ ኣበይት ሕጎች ኣብሮ የመስራት ጅማሮ ማሳየት ኣለብን። የጓደኝነት ይሉኝታ ኣስወግደን ዘላቂ ሃገራዊ ራኢይ ውስጥ እንሳተፍ።
ታደሰ ገብረስላሰ

Ze-Habesha

posted by Tseday Getachew

በዓለም ዓቀፍ የሴቶች ቀን ዝክር፤ በእህቶቻችን ኮርተናል! (ግንቦት 7)

 

Ginbot 7 weekly editorialለዘንድሮው ዓለም ዓቀፍ የሴቶች ቀን መታሰቢያ በአዲስ አበባ ከተማ በተደረገው የሩጫ ትዕይንት ላይ ወጣት ሴቶች ባሳዩት ልበ ሙሉነት ኮርተናል። የሩጫውን ትዕይንት አስታከው፣ በአብዛኛው የሰማያዊ ፓርቲ አባላት እንደሆኑ የተነገረላቸው ወጣት ሴቶች ለፍትህ፣ ለነፃነት፣ ለህሊና እስረኞች መፈታት እና ለሀገር አንድነት ድምፃቸውን ከፍ አድረገው ጮኸዋል፤ ዘምረዋል። እነዚህ ወጣት ሴቶች በሥርዓቱ ምን ያህል እንደተማረሩ በቃላትም በአካል ንቅናቄም አሳይተዋል። ዘረኛውና ፋሽስቱ ወያኔ ግን “ለምን ተቃወማችሁኝ” ብሎ አስሯቸዋል፤ ከፊሎቹም የደረሱበት አይታወቅም። በእህቶቻችን ቆራጥነት ኮርተናል፤ በወያኔ የፈሪ ዱላ ደግሞ ተቆጥተናል። በ1997 እና 98 “የወላጆቻችን ድምጽ ይከበር” ያሉ ሕፃናትን የጨፈጨፈው ወያኔ በ2006 ወጣት ሴቶችን ከማሰቃየት ይመለሳል ብለን አናምንም። ወያኔ እስካልተወገደ ድረስ የፈሪ ዱላው የማይቀር ነገር ነው።

የወንዶቹን ያህል የተዘገበ አይሁን እንጂ በክፉም በደጉም ሴቶች ያልተሳተፉበት የኢትዮጵያ ታሪክ የለም። የቅርብ ጊዜ ታሪካችንን እንኳን ብናይ በፋሽስት ወረራ ወቅት ኢትዮጵያዊያን ሴቶች በአርበኝነት ዘምተው አዋግተዋል፤ ተዋግተዋል። በተለያዩ ምክንያቶች መዝመት ያልቻሉት ደግሞ በውስጥ አርበኝነት ተሰልፈው የጠላት ምስጢሮች ለአርበኞች እንዲደርሱ በማድረግ ከፍተኛ ጀብዱዎችን ፈጽመዋል። ከፋሺስት ወረራ ወዲህ በነበሩ ዓመታት ውስጥም ለፍትህ እና ለነፃነት በተደረጉ ተጋድሎዎች ሴቶች ጉልህ ተሳትፎ ነበራቸው። በተማሪዎች ትግል ውስጥ ለምሳሌ፣ ወጣት ሴቶች በአመራር ደረጃ በመሳተፍ ትግሉን መርተዋል፤ የሕይወት መስዋዕትነት ጭምር ከፍለዋል። ከዚያ ወዲህም በነበሩት ዓመታት በኢሕአፓ እና ሌሎችም ድርጅቶች አመራርና አባልነት ተሳትፈው ከፍተኛ ተጋድሎ ያደረጉ ኢትዮጵያዊያን ሴቶች ነበሩን። በቅርቡም በምርጫ 97 እንቅስቃሴም የሴቶች በተለይም የወጣት ሴቶች ተሳትፎ ምን ያህል ጉልህ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነውና እናስታውሳለን። ለምርጫ ድምጽ መከበር ወጣት ሽብሬ ደሣለኝን ጨምሮ በርካታ ሴቶች ሕይወታቸውን ሰውተዋል፤ ከዚያ የበለጡት ደግሞ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል። ዛሬም እንደ ርዕዮት ዓለሙ የመሳሰሉ ጀግኖች በወያኔ ወህኒ ቤቶች እየማቀቁ፤ በየእለቱ ሰቆቃ (ቶርቸር) እየተፈፀመባቸው መሆናቸው በሀዘንና በቁጭት እናስባቸዋለን።

በሕዝባዊ እንቅስቃሴዎች ውስጥ የሴቶች ተሳትፎ አስፈላጊነት በመፈክር ደረጃ አንስተን የምንተወው ጉዳይ አይደለም። የሴቶች ተሳትፎ ያልታከለበት ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ግቡም አይመታም፤ ቢመታም ዋጋ የለውም።

ከጥቂት ዓመታት በፊት የተካሄዱትን የሰሜን አፍሪቃና የመካከለኛው ምሥራቅ አብዮቶችን በአንክሮ የተከታተለ ማንኛውም ሰው ከሚገረምባቸው ነገሮች አንዱ ሴቶች ያሳዩት ቆራጥነት እና ያካሄዱት ብስለት የተሞላው ትግል ነው። በቱኒዚያ የወጣቶች እንቅስቃሴ ውስጥ ወጣት ሴቶች ከመጀመሪያው ጀምሮ የአመራር ቦታ በመያዝ ተሳትፈዋል። በግብጽም የወጣት ሴቶች እልህ ከወንዶቹ በልጦ ታይቷል። አሁን በዩክሬን ውስጥ የምናየው ሀቅም ይህንኑ የሚያረጋግጥ ነው።

የሴቶች በሕዝባዊ አብዮቶች በስፋት መሳተፍ ከቁጥር ማብዛት እጅግ የላቀ መሠረታዊ ጠቀሜታዎች አሉት። ጥቂቶቹን እንደሚከተለው መዘርዘር ይቻላል።

1.ለሴቶች ያልተመቸ ሥርዓት ለማንም አይመችም። ለማኅበረሰብ በጠቅላላ የሚመች ሥርዓት መገንባት ማለት በቅድሚያ ለሴቶች የሚመች ሥርዓት መገንባት ማለት ነው። ይህ ሥርዓት ደግሞ እነሱ እራሳቸው እየተሳተፉበት፤ ከዚያም አልፎ እየመሩትም ነው መገንባት ያለበት።

2.ሴቶች ከወንዶች በላይ ታጋሾች ናቸው፤ ሲያመሩ ደግሞ በቀላሉ አይመለሱም ተብሎ ይታመናል። እናም የሴቶች በተቃውሞ ትግል ውስጥ በብዛት መሳተፍ ሥርዓቱ በሕዝቡ ምን ያህል እንደተጠላ ግልጽ አመላካች ነው።

3.የወጣት ሴቶች በድፍረት ለተቃውሞ አደባባይ መውጣት ወጣት ወንዶችን ያጀግናል። የወጣት ወንዶች መጀገን ደግሞ ወጣት ሴቶቹን ይበልጥ ያጀግናል። ወጣት ሴትና ወንዶች በእርስ በርስ አርዓያነት ይጀጋገናሉ። እናም ወጣት ሴቶች አምረው ተነሱ ማለት ሁሉም ወጣቶች ሁሉ አምረው ተነሱ ወደማለት ያመራል።

4.የእናቶች መቁረጥ አባቶችን ያነሳሳል፤ የእናትም የአባትም መነሳት ደግሞ መላው ቤተሰብ በሥርዓቱ ላይ እንዲነሳ ያደርገዋል። እናም እናቶች አመረሩ ማለት መላው ቤተሰብ አመረረ ማለት ይሆናል።

5.የሴቶች በትግል አመራር ቦታ ላይ መገኘት በተቃዋሚዎች መካከል ኅብረትን፣ መተሳሰብን ባጠቃላይም ቤተሰባዊ ስሜት ይፈጥራል።

6.ሴቶችና ወንዶች አብረው ሲቆሙ ነው የመተባበር ጥቅም በጉልህ የሚታየው!

የእህቶቻችን በድፍረት ድምፃችሁን ማሰማት ያለው ትርጉም ከድምፃችሁ ከፍታ እና ከቁጥራችሁ በላይ ነው። ዛሬ ጥቂት እንኳን ብትሆኑ ነገ ብዙዎቻችን አርዓያነታችሁን እንድንከተላችሁ ያደርገናል። እናም እህቶቻችን በአዲስ አበባ ጎዳናዎች ባሳያችሁን ድፍረት ተበረታተናል። ኢትዮጵያ ብሩህ ራዕይ ያላት፤ ቆራጥነትን የተላበሱ ወጣቶች ያሏት መሆኑን አሳይታችናል። ይህ ትንሽ ጅምር የትልቅ ሕዝባዊ ማዕበል መንገድ አመላካች ነው።

ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ ዘረኛውንንና አምባነኑን ወያኔ ከጫንቃችን ለማውረድ በምናደርገው ትግል የእህቶችና የእናቶች ተሳትፎ ወሳኝ እንደሆነ ያውቃል፤ ስለሆነም ሴቶች ትግሉን በስፋት እንዲቀላቀሉ ጥሪ ያደርጋል። ሴቶችና ወንዶች፤ ወጣቶችና አረጋዊያን ሁላችንም የወያኔን ዘረኛ አገዛዝን እንዲያበቃ በጽናት እንታገል።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

posted by Tseday Getachew

የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ተጨማሪ አራት ቀን እስር ቤት እንዲቆዩ ተደረገ

Blue Party’s executives and female members

Semayawi Party- Ethiopia

ባለፈው ሰኞ ፖሊስ መረጃ ለማሰባሰብ በሚል ፍርድ ቤት የ14 ቀን ጊዜ ጠይቆ 5 ቀናት እንደተፈቀደለት ይታወቃል፡፡ ዛሬ መጋቢት 5 ቀን 2006 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ፍርድ ቤት የካ ምድብ ችሎት ቢቀርቡም ፖሊስ አሁንም ‹‹ምርምራውን አልጨረስኩም፣ ተጨማሪ የምይዛቸው ሰዎች አሉ፣ የተያዙትም ቢለቀቁ ሌላ ወንጀል ይሰራሉ›› በሚል ሰባት ተጨማሪ ቀናት እንዲሰጡት ጠይቋል፡፡

በአንጻሩ የታሳሪዎቹ ጠበቃ ሆነው የቀረቡት የጋዜጠኛ ርዕት አለሙ አባት አቶ አለሙ ጌደቦ በበኩላቸው ፖሊስ ተሰጥቶት የነበሩት ሰባት ቀናት መረጃ ለማሰባሰብም ሆነ ሌሎች የምይዛቸው ተጨማሪ ሰዎች አሉ ያላቸውን ቢኖሩ ኖሮ ለመያዝ በቂ እንደነበር አስረድተዋል፡፡ በተጨማሪም ታሳሪዎቹ በኃላፊነት ቦታ ላይ የሚሰሩና ቋሚ አድራሻ ያላቸው በመሆኑ በዋስ ተለቀው ጉዳያቸውን መከታተል ስለሚችሉ የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅላቸው ተከራክረዋል፡፡Semayawi party activist court show up

በሌላ በኩል ታሳሪዎቹ በምርመራ ወቅት በፖሊስና ‹በደህንነቶች› እየተፈጸመብን ነው ያሉትን በደል ለፍርድ ቤቱ አቅርበዋል፡፡ ‹‹የታሰርነው በያዝነው አስተሳሰባችን ምክንያት ነው›› ያለው የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ተክለያሬድ መታወቂያ ለማሳየት ፈቃደኛ ያልሆኑ ሲቪል የለበሱ ግለሰቦች ‹‹ሰማያዊ ከሚባል አሸባሪ ወጥታችሁ ከእኛ ጋር ካልሰራችሁ መቼ እንደምንገላችሁ አታውቁም፡፡›› በሚል እንዳስፈራሩዋቸው ገልጸዋል፡፡ በተመሳሳይ ወንድ ፖሊሶች ሌሊት ሴቶች እስር ቤት ውስጥ በመግባት እንደሚያስፈራሩዋቸውም ተገልጻል፡፡ ሴቶቹ ታሳሪዎች ከሌሊቱ ሰባት ሰዓት ላይ ወንድ ፖሊሶች ከታሰሩበት እያስወጡ እንደሚያስፈራሩዋቸውም የየራሳቸውን አጋጣሚዎች ለፍርድ ቤት አቅርበዋል፡፡ ወጣት አቤል ‹‹ከእኛ ጋር ከሰራህ የተሻለ እንከፍልሃለን›› ብለውኝ አልፈልግም በማለቴ እንገልሃለን ብለውኛል በማለት ገልጹዋል፡፡

በተቃራኒው ፖሊስ ተጠርጣሪዎቹ ሌሎች ታሳሪዎች ላይ ቅስቀሳ እያደረጉ መሆኑን፣ በጋራ እንደሚዘምሩ፣ ቃል ለመስጠት ፈቃደኛ እንደማይሆኑ በመግለጽ ተጨማሪ 7 ቀን እንዲሰጠው በድጋሜ ጠይቋል፡፡ ዛሬ ጠዋት ወደ ችሎት ሲመጡ የታላቁን ሩጫ ቲሸርት ካለበስን አንሄድም ማለታቸውንም ታሳሪዎቹ በቀጣይነትም ወንጀል ሊሰሩ ይችላሉ ለሚለው መከራከሪያው እንደ ማስረጃ አቅርቧል፡፡ ዳኛው ፖሊስ በታሳሪዎቹ ላይ እንዳደረሰው የተገለጸውንና ታሳሪዎቹ ሌሎች ታሳሪዎችን በማቀስቀስና በመረበሽ ያቀረበውን ክስ ላይ ምክር አዘል መልዕክት ካስተላለፈ በኋላ ተጨማሪ 4 ቀን የምርመራ ጊዜ ሰጥቷል፡፡

ችሎቱ መደበኛ ስራውን ይጀምራል ከተባለበት አንድ ሰዓት ዘግይቶ ሊጀምር ችሏል፡፡ በክርክሩ ወቅት መረዳት እንደተቻለውም ጠዋት ታሳሪዎቹ ወደ ፍርድ ቤት በሚመጡበት ጊዜ በሩጫው ዕለት ለብሰውት የነበረውን የታላቁን ሩጫ ቲሸርት መልበሳቸውን ፖሊስ በመቃወሙ በነበረው አለመግባባት መዘግየቱ እንደተከሰተ ታውቋል፡፡

ፖሊስ ሰኞ ዕለት ያስመዘገበው የክስ ጭብጥ እንደሚያመለክተው ተጠርጣሪዎቹን በቁጥጥር ስር ያዋለው ሁከትና ብጥብጥ ለመፍጠር ተንቀሳቅሰዋል፣ የጣይቱ ልጆች ነን፣ የምኒልክ ልጆች ነን፣ ዳቦ ራበን፣ ብለዋል በሚል ነው፡፡ በዛሬው የክርክር ሂደት እንደተስተዋለው ግን ፖሊስ የመጀመሪያዋን ጭብጥ ብቻ መዝዞ ተከራክሯል፡፡ መርማሪ ፖሊሱ በወቅቱ አሉኝ ያላቸውን የክርክር ነጥቦች በሚያስረዳበት ወቅት አለመረጋጋት ጎልቶ ይታይበት እንደነበር ተስተውሏል፡፡

http://ecadforum.com/

posted by Tseday Getachew

“በሐረር ከተማ በደረሰው ቃጠሉ ከዛም የክልሉ ፖሊስ በንጹሃን ዜጎች ላይ ጉዳት ማድረሱን በቸልታ አንመለከተውም” – አንድነት

ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ(አንድነት) የተሰጠ መግለጫ

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ(አንድነት)
UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
በሐረር ክልል ሕዝብ ላይ የደረሰውን ከፍተኛ ጉዳት አንድነት በቸልታ አይመለከተውም

የካቲት 30 ቀን 20006 ዓ.ም በታሪካዊቷ የሐረር ከተማ በጀጎል ሸዋበር በደረሰው ቃጠሎ እና ከዚያም በኋላ የክልሉ ፖሊስ በወሰደው እርምጃ በዜጎች ላይ ጉዳት መድረሱ የፓርቲያችንን አመራሮች፣ በሀገር ውስጥ እና ከሀገር ውጪ ያሉ አባላትና ደጋፊዎችን በእጅጉ አሳዝኗል፡፡

ምንም እንኳን የቃጠሎው መንስኤ ተጣርቶ ይፋ ያልተደረገ ቢሆንም በጀጎል ሸዋ በር እየደረሰ ያለው ተደጋጋሚ ቃጠሎ ድንገቴ ነው ለማለት የሚያስደፍር አይደለም፡፡ በተለይም በየካቲት 30 ቀን 2006 ዓ.ም የተነሳውን ቃጠሎ በተገቢ ፍጥነት ለመቆጣጠር የክልሉ መንግስት ፍላጎት ያልታየበት መሆኑ፤ ይልቁንም ግሬደር መኪና አስጠግቶ ቦታውን ለማፅዳት መሞከሩ አጠያያቂ ነው፡፡ የክልሉ መንግስት ቃጠሎውን ለመቆጣጠር ተገቢውን ሁሉ ባለማድረጉ የጉዳቱ ሰለባ የሆነው ህዝብ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ሆኖበት ክፉኛ እንደ ተማረረ በዚሁ ምክንያትም ቁጣ ተቀስቅሶ ፖሊስ በአካባቢው ነዋሪዎች ላይ ጉዳት ማድረሱንም በክልሉ የሚገኙ የፓርቲያችን አመራሮች መረጃውን አድርሰውናል፡፡

በመሆኑም ፓርቲያችን የክልሉ መንግስት ትክክለኛው የቃጠሎ መንስኤ በአስቸኳይ ተጣርቶ ለህዝብ ይፋ እንዲያደርግ፤ በማንኛውም ምክንያት ኃላፊነታቸውን በብቃት ያልተወጡ የመንግስት ኃላፊዎች በግልፅ ለተጠያቂነት እንዲቀርቡ፤ የክልሉ ፖሊስ በህዝቡ ላይ የወሰደው የኃይል እርምጃ በገለልተኛ አካል ተጣርቶ ይፋ እንዲደረግ፤ የክልሉ ፖሊስ በወሰደው የኃይል እርምጃ ጉዳት የደረሰባቸው ዜጎች ብዛትና የጉዳቱ መጠን በአስቸኳይ ለህዝብ ይፋ እንዲደረግ ተገቢ ህክምና እና ካሳ እንዲከፈላቸው፤ ይህንን የፈጸሙ አካላትም ለፍርድ እንዲቀርቡ በአጽንኦት እንጠይቃለን፡፡

በአንድነት ፓርቲ በኩል ይህንኑ በህዝብ ላይ የደረሰ ጉዳት ለማጣራትና ለመከታተል በስራ አስፈጻሚው አስቸኳይ ግብረ ኃይል ተቋቁሟል፡፡ ግብረ ኃይሉ ወደ ቦታው በማቅናት ጉዳዩን ካጣራ በኋላ የደረሰበትን መረጃ እና በፓርቲያችን የሚወስደውን ተጨማሪ አቋም በተመለከተ በቅርቡ ለህዝብ ይፋ እናደርጋለን፡፡

ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር
መጋቢት 4 ቀን 2006 ዓ.ም

Ze-Habesha

posted by Tseday Getachew

በአሜሪካ የሚኖረው የሕወሐት ወንጀለኛ – ከኢየሩሳሌም አርአያ

 

 

The Ethiopian author, former TPLF torture czar and spymaster “Professor” Bisrat Amare

Bisrat Amare former head of TPLF Intelligence

የሕወሐት አባል የሆነውና በአሜሪካ የሚኖረው ብስራት አማረ በርካታ ወንጀሎችን እንደፈፀመ የቅርብ ምንጮች አጋለጡ። ሕወሐት በረሃ እያለ የባዶ 6 እስር ቤት ዋና ሃላፊ የነበረው ብስራት አማረ የኢ.ህ.አ.ፓ አባላት የነበሩት እነ ፀጋዬ ገ/መድህን (ደብተራው) ጨምሮ በሕወሐት የተያዙትን በሙሉ ወረኢ ተብሎ በሚጠራው ስፍራ በነበረ እስር ቤት በጅምላ አሰቃይቶ እንደገደላቸው ምንጮቹ አረጋግጠዋል። በሺህ የሚቆጠሩ የትግራይ ሰዎች « ኢዲዩና ፊውዳል..» በሚል ባዶ 6 ተብሎ ይጠራ በነበረው እስር ቤት ተሰቃይተው እንዲገደሉ የተደረጉት በብስራት አማረ መሆኑን የጠቆሙት ምንጮቹ ከዚህ በተጨማሪ የድርጅቱን በርካታ አባላት እንዳስገደለ አያይዘው ገልፀዋል። እነተክሉ ሃዋዝ በዚህ ወንጀለኛ ከተገደሉት ይጠቀሳሉ ሲሉ ያክላሉ። በ1983ዓ.ም ሕወሐት/ኢህአዴግ አገሪቱን ከተቆጣጠረ በኋላ የሟቹ የደህንነት ሹም ክንፈ ገ/መድህን ምክትል የነበረው ብስራት አማረ ከቤተ መንግስት የጃንሆይ የነበረ ከፍተኛ ወርቅ በመዝረፍ መውሰዱን ያጋለጡት ምንጮቹ በዚህ የዘረፋ ወንጀል ሆለታ እስር ቤት እንዲገባ መደረጉን ያመለክታሉ። በነስብሃት ነጋና መለስ ዜናዊ ትእዛዝ እንዲፈታ ተደርጐ ወደ አሜሪካ የተሸኘው ብስራት አሜሪካ ሲጓዝ የዘረፈውን ወርቅ ይዞ እንደነበረ ጉዳዩን በቅርብ የሚያውቁ ምንጮች በግርምት ይገልፃሉ። ብስራት አማረ አሜሪካ ከመጣ በኋላ ቅርስ የሆኑትንና የዘረፋቸውን ወርቆች መሸጡንና አንዲት ሴት ለማሻሻጥ የተቀበለችውን 1ኪሎ ወርቅ ከወሰደች በኋላ እንደካደችው ማወቅ ተችሎዋል። ብስራት አማረ ስለዚሁ ጉዳይ ተበሳጭቶ የነገራቸው ምንጮች ማረጋገጫ ይሰጣሉ። የብስራት ታናሽ ወንድም የሆነውና በደህንነት ቢሮ ይሰራ የነበረው ታጋይ ጠስሚ (ጠስሚ -ትርጉሙ ቅቤ ማለት ነው) ከስራው በመልቀቅ የአስመጪና ላኪነት ትልቅ ቢዝነስ መክፈቱን የጠቆሙት ምንጮቹ አክለውም፥ ድርጅቱ የተከፈተው ብስራት አሜሪካ ከገባ በኋላ በላከለት ገንዘብ መሆኑን አስታውቀዋል። (ስለዚሁ ጉዳይ በ1995 ዓ.ም በኢትኦጵ ጋዜጣ መረጃው ይፋ መደረጉና የብስራት ወንድም ቅቤ ኢትኦጵ ቢሮ ድረስ በመምጣት የጋዜጣውን አዘጋጅ በድንጋጤ ተውጦ “የራሴን ቢዝነስ ተቋም ነው፤ እነማን መረጃ እንደሚሰጧችሁ አውቃለሁ። እባካችሁ የእኔንም፣ የወንድሜንም ስም አታንሱ?” በማለት ተማጽኖ አቅርቦ ነበር።) ብስራት አማረ ከሽማግሌው ስብሃት ነጋ ጋር ባለው የጠበቀ ግንኙነት ወደ ኢትዮጵያ ሲመላለስ መቆየቱን ያወሱት ምንጮቹ፣ ወንጀለኛውና ዘራፊው መቀሌ ሄዶ አስገደ ገ/ስላሴን እንደከሰሰ አስታውቀዋል። የደርግ ወንጀለኞች ከአሜሪካ በገዢው ፓርቲ እየተወሰዱ ነገር ግን የኢ.ህ.አ.ፓ አባላትንና ሌሎች ንጹሃን ዜጎችን በጅምላ የፈጀና የአገር ቅርስ የዘረፈ ወንጀለኛ ጠያቂ ማጣቱ አስገራሚ ነው ብለዋል ምንጮቹ። ጠያቂ አካል ካለ በወንጀለኛው ብስራት አማረ ላይ ለመመስከር ፈቃደኛ መሆናቸውን አክለዋል። ይህን ምስክርነትና ማረጋገጫ ሊሰጡ የሚችሉና በአሜሪካ የሚኖሩ ሶስት የቀድሞ የሕወሐት ሹሞች እንዳሉና የብስራትን ወንጀል ጠንቅቀው የሚያውቁ መኖራቸውን አያይዘው ጠቁመዋል።

http://ecadforum.com/

posted by Tseday Getachew

አሜሪካ የበለጠ ትናገር! (ከጸጋዬ ገ/መድህን አርአያ)

 

ከጸጋዬ ገ/መድህን አርአያ

ነፃነቴን ካልሰጣችሁኝ ሞትን እመርጣለሁ

ፓትሪክ ሔንሪ Give me Liberty or Give me Death

ፍሬደሪክ ዳግላስ (1818- 1895) ከባርያ እናትና ከነጭ አባት የተወለደና ራሱም ቢሆን በቦልቲሞር (ሜሪላንድ) የቤት አሽከር ሆኖ የቆየ ሰው ነበር። አንድ ማለዳ ጁላይ 4 ቀን 1852 ን ተንተርሶ (አንተርሶ) በሮቼስተር ከተማ (ኒውዮርክ) ንግግር እንዲያደርግ ጥሪ ይደርሰዋል። ደብዳቤው ሲደርሰው እንደ እብድ ከራሱ ጋር መነጋገር ያዘ። መቸም አንዳንድ ጊዜ እንዲህ ያለ ለማመን የሚከብድ አጋጣሚ ሲመጣብህ ናላህ ይበጠበጣል። ፍሬደሪክ ዳግላስም “በእርግጥ ይህ ደብዳቤ ለእኔ የተጻፈ ነው? የተቀባይ ስምና አድራሻ ስሕተት ተፈጽሞ ይሆን?” ሳይል አልቀረም። ዳግላስ በዚህ ዓይነት ሁኔታ ጭንቅላቱን ሲበጠብጥ ቆይቶ ትንሽ አረፍ አለ። ሲነቃ ይኸ ዕድል እንዳያመልጠው ፈለገ። ይልቁንም የሚናገርበት ርዕስ መጣለት። “ በመሰረቱ እኔን ባርያውን በዚህ በዓል ላይ እንድገኝ- ለዚያውም ተናጋሪ መሆኔን ሳስበው ይህ ሁሉ ግብዝ- የግብዝም ግብዝ ነው አለ። ይበልጥ ደግሞ ለተሰብሳቢው ስለጁላይ 4 (ነፃነት በዓል) እንድናገር እኔን ባርያውን መጋበዛቸው ሌላው ግብዝና ነው ” አለ። ለማንኛውም ንግግሩን አዘጋጀ። በዚያ ወቅት በሮቼስተር ከተማ ያደረገው ንግግር እስከ ዛሬ ድረስ ከዓለም ታላላቅ ዲስኩሮች አንዱ ለመሆን በቅቶአል። “ጁላይ 4 ቀን ለመሆኑ ለባርያው ምኑነው? What to the Slave is the Fourth of July?

ዛሬ ከብረት በከበደ ክንድ ኢትዮጵያን እየገዙአት የሚገኙት ጌቶች- አዳዲስ መሳፍንት- አዳዲስ መኳንንት፣ አዳዲስ ዲታዎች…የንግስ በዓል ከሳምንታት በኋላ ይከበራል። (በዩጐዝላቩ ጂላስ The New Class, ወይም ከሮማውያን ዘመን አንስቶ Nouveau Riche ቀላል ድግስ አያውቁም። ስለዚህ ጉንበት 20 ቀን በታላቅና ታይቶ በማያውቅ ድምቀት ይከበር ዘንድ ዝግጅቱ እየተሟሟቀ ነው። አገር ያፈራው ትልልቁ የሐረር ሰንጋ፣ ወደል ወደል የሚያክለው የወለጋ ላታም በግ ወዘተ ተመርጦ ተመርጦ ይቀርባል። ሻምፓኙ፣ ውድ ውዱ አይሪሽ መጠጥ- ዊስኪ፣ ድራንቡዬ፣… የፈረንሳይ ኮኛኮች፣ ምርጥ ወይን ጠጆች..ያልፍላቸዋል። ምንም ማጋነን የለበትም። ጫካ ውስጥ በነበሩበት ጊዜ እንኳ ለድግስ ስንትናስንት ሚሊዮን ብር ሲያወጡ እንደነበረ ከጉያቸው የወጣው ጠንካራ ኢትዮጵያዊ…ገብረ መድኅን አርአያ ገልጦታል።

“ኑና ጉንበት 20ን አብረን እናክብር” ተብለው የተጠሩ ወይም እንጠራለን ብለው ቀኑን እንደወላድ እየቆጠሩ- የራቀባቸው ሰዎች የሉም አትሉም። እናንተም እንደኔ። ከውጭ የሚጋበዙ በርካታ ሰዎች ይኖራሉ። አዳራሾች-ሆቴሎች- በየደረጃው… ላይበቁ ነው። እሸሸ ገዳሜው፣ አስረሽ ምቺው ደግሞ የሚጠበቅ ነው። ስለገዢዎቻችን ሀብትና ንብረት ያልተባለ ነገር የለም። ይኸ ደግሞ የሞራሉን ቁልቁለት ምንኛ እንደ ተያያዙት ስም እየጠቀሰ መረጃ የሚሰጠንን ውስጥ አወቅ ኢየሩሳሌም አርአያን ማድነቅ እወድዳለሁ። በሽምግልናና ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ በሚገባቸው ዕድሜ የእኝኝ ብላ ባዝራዎች፣ አንድና ሁለት (በቀን) የማይበቃቸው የወንድ መለኮኖች አሉባቸው። ከዚህ ተራ ውስጥ ሁለት ሰዎችን ብቻ (በረከተ-መርገም ስምዖንና ስዬ አብርሃ) ነፃ ያወጣቸው ደግሞ ተስፋዬ ገብረ-አብ ነው። ስለሆነም ዳንኪራውና ስድ የሆነው በዓል የሚጠበቅ ነው። እኛም የኢትዮጵያ ጉስቁሎች የሌላ ሕዝብ በዓል በሥነ ሥርዓት መጠበቅ አለብን። የበዓሉን መንፈስ ማደፍረስ፣ ማደናቀፍና ማቃወስ በአሸባሪነትና በመሳሰለው አንቀጽ ያስቀጣል። አዎን ጉንበት 20 ቀን የድግሦች ድግሥ፣ አውራ በዓልና የድግሦችና የበዓሎች ሁሉ እናት ናት። ማን ያውቃል? ድሮ ጃንሆይ አጤ ኀይለ ሥላሴ ሐምሌ 16ን “የትዮጵያ የልደት ቀን” እንዳሉአት እነዚህ አዳዳሶቹ መሳፍንትም ጉንበት 20ን “እውነተኛው የኢትዮጵያ ናጽናት ቀን” ቢሉት አይደንቀኝም። ( ብቻ ማን ነበር- የአንዱ ሕይወት የሌላው መርዞ ነው- ያለው?)let America speak

በአገራችን የድግስ ነገር ሲነሳ ትንሽ የማስታውሳቸው ነገሮች አሉ። በአጤው ጊዜ ጃንሆይ የተወለዱበት (ሐምሌ16) እንዲሁም የነገሱበት (ጥቅምት 23) ይከበሩ ነበር። ለኢትዮጵያ ባሕልና ፖለቲካ እንግዶች የሆናችሁ ወጣቶች ምናልባት አታውቁት ይሆናል እንጂ በክብርም ቢሆን ቤተ መንግስት ስትጠሩ ግርግሩ ብዙ ስለሆነ ትንሽ ጨፈቃ ትቀምሳላችሁ። እንጀራው በእግር የተቦካ ነው ይባላል። ለማንኛውም “የንጉስ በረከት” አይናቅም ትባላላችሁ። (ይህንን የበለጠ ለማወቅ ፍቅር እስከ መቃብርን ያነብቡአል) ወደኋላ ጊዜ የሐምሌ 16 በዓል አከባበር ለአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት ተሰጥቶ ነበር።

የድግስ ነገር- በመንግስት ሰፈር- ብዙ ምልኪ አለበት። ስለ ጃንሆይ መንግስት አወዳደቅ ብዙ ቢባልም ለጊዜው አንዱን አነሳለሁ። አንዳንድ ሚኒስትሮች እጅግ ከቅብጠትም ባሻገር ስለሄዱ ክራር ይዘው ወደ መሸታ ቤት መሄድ አብዝተው ነበር። የዛሬዎቹ ከእነዚያ ጋር ባይወዳደሩም ትንሽ ትንሽ ሕዝብንና አኗኗሩን ወደ መርሳቱ ደርሰው ነበርና ሌላው ቀርቶ ከመሳፍንቱ አንዱ የነበሩት ጄኔራል ዐቢይ- “አውቀን እንታረም” የሚል መጽሐፍ ደርሰው ነበር። ጠንቃቃው ጄኔራል “አውቀን ካልታረምን ሌላው ቀርቶ ሬሳችን እንኳ የወደቀበት አይታወቅም” ብለው ነበር። አዎን አርማጌዶን በዓለም ፍጻሜ ላይ የሚከሰት ሳይሆን ያልታሰበ የእልቂት መውረድም አርማጌዶን ሊባል ይችላል። ያ ወቅት የሞራል ድቀት ሥጋና ደም ገዝቶ የሚታይበት፣ ሕዝብ ሲያልቅ አንዳንድ ሹማምንት መንደላቀቅ ያበዙበት ነበር። ደርግ ጃንሆይን ከሥልጣን ሲያወርድ “ሕዝብ በሺህ ቤት ሲረግፍ እነሱ በእሸሸ ገዳሜ ተጠምደው…” እያለና የቀለጠ ድግስ በቴሌቪዥን እያቀረበ ነበር። ድግስ….

ደርግ ራስዋ በራስዋ ያመጣችው ጣጣም አለ። ወደ ሥልጣን የመጣበትን ቀን ለማክበር ብልጭልጩንም ማናምኑንም ሰልፉንም…ሲያበዛ የእንግሊዝ ጋዜጠኞች በሁለት መቶ ሺህ ዶላር ውስኪ ሸጥን አሉና…የደርግ መሰላል ወደታች ብቻ የሚያወርድ ሆነ። ድግስ እየተኮነነ መጣ። ድግስ እየተጠቀሰበት ወረደ። ሁለት መቶ ሺህ ሕዝብ በረሃብ አለቀ ብሎ ተሳለቀ ተባለ። በራሱ ጊዜ ዘጠኝ ሚሊዮን ሕዝብ ተርቦ ውስኪ ተራጩ ተብሎ ለወያኔ ፕሮፖጋንዳ ተመቸ። እዚህ ላይ ያነሳሁት የጉንበት 20 አከባበር ያንኑ እድል ይከተል ይሆናል- ይከተላልም- ቁልቁለቱን ጀምሮአል በሚል ነው። ድግሶች በሦስቱ መንግስታት- የሥልጣን መልቀቂያ ጊዜ ምልክቶች- ብልሽትሽቱ የወጣ መንግስት ማክተሚያ ወቅቶች ሆነው አይተናቸዋል። ( ሁሉም የእጁን ያገኛል- ብድሩን ወይም ብድራቱን ተከፈለ- በሰፈሩት ቁና መሰፈር አይቀርም የሚባል አነጋገር ያለ ይመስለኛል። የእንግሊዝኛው ፈሊጥ ግን Poetic Justice ይለዋል) “ያርግላቸው!” አሜን ያድርግላቸው!!

ደርግ የተወነጀለበት 200ሺህ ዶላር ዛሬ አንድ ባለ ጊዜ ወያኔ ለልጁ ልደት ከሚደግሰው በታች ነው። በ1997ዓ.ም አባዱላ ገመዳ ለልጃቸው ዘኪያስ አባዱላ 24ኛ ልደት በዓል የ100ሺህ ዶላር ኮብራ ዘመናዊ መኪና በስጦታ መልክ አበርክተዋል። በ1994ዓ.ም በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ 14ሚሊዮን ሕዝብ ለረሃብ ተጋልጦ ነበር። መለስ ዜናዊ ከ10 ዓመት በኋላ “በቀን ሶስት ጊዜ ትበላላችሁ” ባሉበት ዓመት መሆኑ ነው። የመለስ ዜናዊ መንግሥት ለተራቡት ወገኖች ደንታ አልነበራቸውም። በድርጅታቸው የተፈጠረው ቀውስ ላይ በማተኮርና ለእርሳቸው የሥልጣን ዕድሜ ማራዘሚያ ሲሉ “ተሃድሶ” ብለው ለሰየሙት ቱማታ 280ሚሊዮን ብር ባጀት መድበው ካድሬዎቻቸውንና ተከታዮቻቸውን በድግስና በውስኪ ያምነሸንሹ ነበር። በዛው ዓመት ልጃቸው ሠማሃል መለስ የልደት በዓልዋን በግዮን ሆቴል ዳስ ተጥሎ አክብራለች። ለኬክ ብቻ ግማሽ ሚሊዮን ብር ነበር ወጪ የተደረገው። የመለስ ልጅ ልደትዋን በምታከብር እለት በግዮን ሆቴል ደጃፍ በርካታ በረሃብ የገረጡ ወገኖች የሚላስ የሚቀመስ አጥተው ወድቀው ነበር።

ስለ ድግስ ዝርዝር ለመጻፍ ፍላጐቱ የለኝም። ደግሼም አላውቅም። መንግስት ሲቀናጣ፣ እሸሸ ገዳሜው ልክ ሲያጣ፣ የሞራል ድጡ መጠነ ቢስ ሲሆን፣ ሰብአትካትን- ሰዶምና ገሞራን ወይም የጥፋት ውሃን ዘመን ሊያመለክተን ይችላል። ራስ ተፈሪዎች “ባቢሎን” ይሉታል። እንዲያውም በቀድሞው መንግስት በጠቅላይ ሚኒስቴር ሚኒስትር የነበሩት ዶክተር ሥዩም ሐረጐት The Bureaucratic Empire, Serving Emperor Haile Selassie በሚለው መጽሐፋቸው ያነሱት አንድ ነጥብ ስለድግስና ስለመሳሰሉት ጉዳዮች ነበር። ኮረኮረኝ። ሥዩም ሐረጐት እንደጻፉት የቀ.ኀ.ሥላሴ ባለስልጣኖች የታሰሩት ጠጅ ለመጣል ምቹ ቅዝቃዜ በነበረው ሥፍራ ነበር። ከላይ የደርግ አባላት ስብሰባ ሲካሄድ፤ ሑካታ ሲፈጠር፣ ጭብጨባ ሲበዛ ወዘተ በእሥረኞቹ ላይ ይፈጠር የነበረውን የመንፈስ ጭንቀት ይነግሩናል። አሳሪዎች የእሥረኞች ሥቃይ ሊታያቸው ከቻለ በእርግጥ “ሰው” የመባል ሙሉ ባሕርይ አላቸው ለማለት ይቻላል። (የደርጉን ዘመን ግፍ ለማውራት የምደፍርበት ወኔ የለኝም። ራሳቸውን እየቀደሱ በሌሎች ግለሰቦች ላይ ከሚደነፋፉም ጋር ጠበል የምጠጣ አይደለሁም። አንድ ነገር ላይ ከተስማማችሁልኝ ደርግ በውሃ አጥምቆ ቢሆን ወያኔ ይኸውና በእሳት እያጠመቀ ይገኛል። የጥምቀቱ ተቀባይ ደግሞ መላው ወገኔ ነው።)

የአሜሪካ መንግሥት ባለፉት ቀናት የኢትዮጵያን ድንኳን ገለጥለጥ አድርጐ የአገሪቱን የሰብአዊ መብት አጠባበቅ፣ የፖለቲካ እሥረኞች አያያዝ፣ በገጠር ያለውን ብሔረሰቦችን የመከፋፈል መንግስታዊ ጫናና ወንጀል አሳውቆናል። አሳውቆልናልም። በመላው ኢትዮጵያ የሚገኙ ሰማንያ ሺህ የፖለቲካ እሥረኞች አሉ። ከእነዚህም መካከል ስድሳ ከመቶው አእምሮ እስከ መሳት መድረሳቸውን በምስክርነት አቅርቦልናል። ዝርዝሩ ብዙ ነው። ታላቅ ወንድም (የተጠጋኸው ትልቅ መንግሥት በፖለቲካው ቋንቋ ቢግ ብራዘር ይባላልና) ምናልባትም የእሥረኛውን ቁጥር ቀንሶት ይሆናል እንጂ በኢትዮጵያ እየኖረ ወያኔንና ትውልደ ወያኔ ያልሆነ ለመሆኑ ያልታሰረ – አለዚያም እሥራት የማያስጨንቀው ማነው? ብለው የሚጠይቁ የትየለሌ ናቸው። ያልታሰሩ የሚመስላቸው ሰዎች ደግሞ የጥርስ ችግር እያለው ሕመም ሳይሰማው በመጨረሻ ላይ አምስትና ስድስት ጥርሶቹ ሲረግፉለት ለቃቅሞ ወደ ሐኪም ቤት እንደሚሮጥ ሰው ናቸው።

እንደሁም ልጆቻቸው ወይም የአገር ወጣቶች በነቂስ እየታረዱ ኅዘኑ ከቤታቸው የማይገባ፣ የቤተሰብ አውራ በባለቤቱ ፊት ታስሮ ሚስት ስትነወር፣ ንብረቱ ሲድፋፋ፣ ጐታው ሲደፋ ልቅሶውና ዋይታው ከጆሮአቸው የማይደርስ ጐረቤት ወገናችን አለ። የድንጋይ ልብ የገባለት። አንዳንድ የማውቃቸው ሰዎች – ጐይትኦም ብቻ ሳይሆን- ደባልቄና አምበርብርም ጭምር – ከውጭ ወደ ኢትዮጵያ ሄደው ሲመለሱ ተመሣሣይ ትዝታ ይዘው ይመጡላቸዋል። አዲስ አበባ ውስጥ የሚሠራው የእድገት ምልክት የሚገለጥ አይደለም። የአለቃ ደስታና የተሰማ ግጽው መዝገበ ቃላት በቂ ቃላት የላቸውም። “እንዲያውም በእንግሊዙ ንገረኝ” ትለዋለህ። አንተም አሿፊ እሱም አሹዋፊ ትባላላችሁ። ጓድ መንግሥቱ ኅይለማርያምን ብጠቅስ እንደማትቀየሙኝ ተስፋ አደርጋለሁ። በኢትዮጵያ ራዲዮ በሠራሁባቸው ዓመታት አንድ ቀን ስለ ራዲዮ አሠራር ስንገልጽላቸው ምርር ትክን ብለው “ ዘፈኑና ጭፈራው አልበዛም ወይ? ለመሆኑ ወገኖቻችን በጠላቶቻችን ሰይፍ እየተመቱ፣ አብዮታዊ ሠራዊታችን በግራም በቀኝም – በሰሜንም በምሥራቅም፣ በመሐል አገር ደግሞ በአምስተኛ ረድፈኞች ጓዶቻችን ሁሉ እተየረሸኑ..እያለቅን አይደለም ወይ? ኢትዮጵያ ራስዋ እንደ አንድ ልቅሶ ቤት መታየት የለባትም ወይ? እንዴት ነው በዚህ ሁሉ ልቅሶኛ ላይ እሸሸ ገዳሜ ዘፈን ለማሰማት ፈቃድ የምትፈልጉት? ፈቃድ የሚጠየቅበት አይደለም። እንደየስሜታችሁ ነው። ደስ ካላችሁ ዝፈኑ። አስዘፍኑ። አለዚያም ዳኝነቱ የእናንተ ነው” ብለው ነበር። አንዱ ሲደሰት ሌላው ያዝናል። ዓለም ጉራማይሌ!

ሕይወት ከዚህ መሠረታዊ አመለካከት ይጀምራል። ግን ከአለቃችን ንግግር ውስጥ ማንንም ሊነካ የሚገባው ለአገራቸው ባበረከቱት ቅንና ሕጋዊ አገልግሎት ምክንያት እንደ ወንጀለኛ ተቆጥረው ወደ ወህኒ ዓለም የተወረወሩትን ሰማንያ ሺህ ኢትዮጵያውያን በዓይነ ሕሊናችሁ ጐብኙልን። አሜሪካ የምትነግረን- የማናውቅወን አይመስለኝም። ራስዋን በምስክርነት አቅርባለች። ከተጠቀምንበት። ወይም ፕሮፌሰር አሥራት ወልደየስ አንድ ሰሞን ይሉ እንደነበረው “በደርግ ጊዜ አሜሪካ በክምር ሳር ውስጥ የወደቀች መርፌ ይታያት ነበር። አሁን ግን በእልፍኝ ውስጥ የቆመው ዝሆን እንዳይታያቸው አንድ ዓይነት ግርዶሽ (ማዮፕያ) ተፈጥሮባቸዋል” አይደለም? ጉዳዩ የኢትዮጵያውን ጉዳይ ነው ተባብለናል። የኢትዮጵያን ዋና ዋና ትግሎች (ጦርነቶች) በቅጥረኛና ካልሆነም በአሜሪካ አማካይነት የምንዋጋቸው አይደሉም። ይልቁንም ዛሬ አሜሪካ የነገረችን ሁላችንም እሥረኝነት እንዲሰማን ይመስላል። ጐበዞቻችን በወህኒ እየማቀቁ ነው።

ስለ እስክንድር፣ ስለ በቀለ፣ ስለ አንዱዓለም፣ ስለ ርእዮት….ሰምተን ነበር? ከእነሱ ሌላ ሰማንያ ሺህ ማን ያውቃል 180ሺህ ሰዎች በወህኒ ዓለም ይማቅቃሉ። ሌሎች ያልታሰሩ ግን “በመተካካት መልክ” ሊገቡ ወረፋ እየጠበቁ ናቸው። አፍጥጦ የመጣብን- እስካሁንም ያልተመለሰው ከባድ ጥያቄ- ለመሆኑ እኛስ አልሞትንም ወይ? መቸም ወደፊት እንደምንተሳሰበው ከሞቱት አንድ ሚሊዮን ሁለት መቶ አምሳ ሺህ ውስጥ አይደለንም ወይ? የመኖር ያለመኖር ማረጋገጫ (ምናልባት ሰርተፊኬት ወይም ሊቸንሳ) አግኝተናልን? ራስ ቢተወደድ መኮንን እንዳልካቸው “አልሞትሁም ብዬ አልዋሽም” ነበር ያሉት? ሙኩሼዬ ጸጋዬ ገብረ መድኅን ቀዌሳ ደግሞ ልዑል ሐምሌት የሚያንበለብለውን ዘላለማዊ ስንኝ እንዲህ ብሎ በከፊል ወደ አማርኛ መልሶታል።

መኖር አለመኖር እዚህ ላይ ነው ምሥጢሩ
የዕድል ፈተና አለንጋ ሲወናጨፍ ወስፈንጥሩ

ይህ ዕድል ያልደረሰውና የፈተናውም አለንጋ ያልገረፈው አለ ወይ? ይለናል። ኦስካር ዋይልድ ይመስለኛል በሶሻሊዝም ሥር የሰው ነፍስ (The Soul of Man under Socialism) ድርሰቱ “መኖር እጅግ ብርቅ ከሆኑ ባሕርያት ዋነኛው ነው። ብዙ ሰዎች እንዲሁ አሉ። ግን አይኖሩም ” ያለው (To live is the rarest thing in the World. Most people exit, that is all ) ይለናል በአንክሮ። የእኔው የትግል አድባር (አያውቀኝም) ፕሮፌሰር ሐጐስ ገብረ ኢየሱስ እናቱን ለመጠየቅ ጓድ መንግሥቱ ሔሊኮፕተር አዘዙለትና ወደ አድዋ ሔዶ ነበር። ሲመለስ A Requiem of History በሚል ያቀረበውን መጣጥፍ አልረሳውም። በዚያው ሰፊ ጽሑፉ ውስጥ እንደ ፈርጥ ያየሁለት “እናቴ በእርግጥ በሕይወት አለች። እየኖረች ግን አይደለም። She was alive, but Not living.” ይላል።

በ1980ዎቹ ካነበብኋቸው መጻሕፍት መካከል በሔንሪ ኪየምባና በዴቪድ ማርቲን የተገለጡ አስደንጋጭ አጋጣሚዎች በአእምሮዬ ውስጥ የተከሉት ክፉ ትዝታ አለ። በኢዲአሚን ኡጋንዳ ጊዜ የተፈጸመ ነው። እንዲያውም የ“State of Blood” የሚለው ጸሐፊ የኡጋንዳ የጤና ጥበቃ ሚኒስተር የነበረው ሔንሪ ኪየምባ ነው። ወደ ወጉ እንመለስና ኢዲአሚን በየቀኑ ሥፍር ቁጥር የሌለው ኡጋንዳዊ የሚገድልበትና የጭፍጨፋው ወፍጮ እንበለ እረፍት የሚሠራበት ሥፍራ ነበር። በዚህ “ሥራ” ላይ የተሰማሩት ባለሙያ ነፍሰ- ገዳዮች ትንሽ ፋታ ካገኙ ወደ ሰፈር መሸታ ቤት ይሄዱና ካቲካላና ቡቅር ከሚመስለው “ነፍስን ጭምር” ከሚያስረሳው መጠጥ ይጨልጣሉ። ግድያው እንደ ጫት ሐራራ ስለሆነባቸው በማይገድሉበት ሰዓት ሁሉ ሲያፋሽጉ ይውላሉ።

አንድ ቀን ያለወትሮው ግድያው በምሽት ሰዓት ሊጠናቀቅ ስላልቻለ ዋናው ገዳይ እስረኞቹን ይሰበስብና “ዛሬ ስለመሸ ሄዳችሁ ከቤተሰቦቻችሁ ጋር እደሩና ነገ በጠዋት መጥታችሁ መቃብራችሁን ቆፍራችሁ ትገደላላችሁ። አሁን ሂዱ። መልካም ዕድል” ይላቸዋል። በማግስቱ እስረኞቹ ተሽቀዳድመው በመሰለፍ መቃብራቸውን ቆፍረው በተሰጣቸው ትልልቅ መዶሻ አንዱ ሌላውን ገደለ ይባላል። ተረት ወይም የፈጠራ ድርሳን አይደለም። ዴቪድ ማርቲን በኦብዘርቨር ጋዜጣ ላይ በተከታታይ ያቀርብ የነበረውን ሐተታና ከላይ በርእሱ ያመለከትሁትን የሔንሪ ኪየምባ መጽሐፍ ያነብቡአል።

ገዥዎቻች፣ አንዱን ጠባብ፣ ሌላውን ነፍጠኛ በማለት የሰየፉት ወገን ቁጥር ይታወቃል? ከምዕራብ ወደ ደቡብ፣ ከደቡብ ወደ ምዕራብ እያንከራተቱ በየኪሎ ሜትሩ የረገፈው ወገናችን ቁጥር ይታወቃል? በአኅዝ የማይገለጠው መከራውና ሰቆቃው በምን ይተመን? እዚህስ ደረጃ አልደረስንም የሚያሰኝ ምን ምልክት አለ? አሁንም ለእርድ የተዘጋጀን ነን- ሁላችንም ባንሆን አብዛኞቻችን። ንጹሐን ዜጐችን ግደሉ ብንባል ዓይናችንን የማንጨፍን አለን። አሁንም ቢሆን እኛን በእኛ እየጨረሱንም እያጫረሱንም ነው። አይደለምን? የኢዲአሚኑ ሪፖርት ይዘገንናልን?

ያንን የምታውቁትን ለፍቶ ያስተማረኝ የኢትዮጵያ ገበሬ ሲባልለት የቆየውን “ናስቲለው”…አልፎ አልፎ ታስታውሱታላችሁ? ትዝ ሲላችሁ ዓይናችሁ እንባ ይቋጥር ይሆን? (ናስቲለው በሰሜን ኢትዮጵያ ገበሬ ማለት ነው።) አሜሪካ ስለ ኢትዮጵያ ገበሬ በመንግስት መሰቃየት ያርዳን? አቦ! አቦ! እንደ ብዕርና ወረቀት ያስጠላኝ ነገር የለም። ካሣ ተሰማ ትዝ አለኝ። ድንቀኛው ጸሐፊ ጓደኛዬ ብርሃኑ ዘሪሁን ካሣ ተሰማን አንድ ቀን አነጋግሮት ነበር። ለመነን መጽሔት ነበር። ብርሃኑ ወርቅ የሆነውን የካሣን ፕሮፋይል ሲያቀርበው “ቧንቧ ሠራተኛው ካሣ” በማለት ነበር። ካሣ ክራር መደርደር የለመደው በስሜት ነው። ከተቃጠለ አንጀቱ የሚያወጣውን ትንፋሽ በዘፈን ለማብረድ ነው። ካሣ ይዘፍናል። ስሜቱ ወደ ጽርሐ-አርያል ይከንፋል። እሱም ራሱ እንደ ማኰብኰብ ሲለው ክራሩን ሰባብሮ ሲጃራ መግዣ ፍለጋ ይሄዳል።

ይኸ ሁኔታ ዛሬ ይገባኝ ጀምሮአል። ከክራሩ ባሻገር የሚሰማው ድምፅ ያለ ይመስለኛል። ከመላእክት ጋር ሲነጋገር ቆይቶስ ቢሆን? ከአድማስ ባሻገር ከታላላቆቹ ተራሮች ላይ ሆኖ ስለዚች አገር ዕድል- ስለሚደርስባት አደጋ፣ ስለ ትንንሽ ልጆችዋ መቀጨት፣ እንደ ዛሬ ስላለው የመከራ ሌሊት ያጫወቱት እንደሆነ ማን ያውቃል? እንዲያ ሆኖ ሆኖ ካሣ ወደ ቧንቧ ሥራው ይመለሳል። እሱም ዘመንን ቆጥሮ ወደ መሬቲቱ ተመለሰ። ወደ ማኅፀናዋ።

እኛንም ደካሞች ልጆችዋንም እነሱንም ባሊጊዜና ቅምጥል አዳዲስ መኳንንትና መሳፍንት የኢትዮጵያ መሬት እኩል ትበላናለች ወይ? ስለ ጄኔራል ደጐል ያነበብሁት አንድ ታሪክ አለ። ጄኔራል ደጐል ሽባ ሆና የተወለደች ልጅ ነበረቻቸው። ወላጆች እጅግ እያዘኑ ልጅቱ በመንፈስ እንድትጠነክር የማያደርጉት አልነበረም። የሚችሉትን ጥረት ሁሉ ካሙዋጠጡ በኋላ ልጅቱ ትሞታለች። እናት መሆን አይቀርምና ማዳም ደጐል ምርር ብለው ያለቅሳሉ። ያዝናሉ። እሳቸውን ማጽናናትም ከባድ ሆነ። በዚህ ጊዜ ጄኔራል ደጐል ባለቤታቸውን “እስካሁን ድረስ ምኞታችንና ጸሎታችን ሁሉ እግዚአብሔር ከሰው እኩል እንዲያደርጋት ነበር። ይኸውና በሕይወት ባይሆን በሞት ከሁሉ ጋር እኩል ሆናለችና ልቅሶሽን ተይ…” በማለት ባለቤታቸውን አጽናኑአቸው።

ኢትዮጵያውያን ሽባ ሆነን አልተፈጠርንም። ወይም አዳዲሶቹ ዲታዎች (ኖቮሪሽ) በአፋቸው ላይ የወርቅ ፍልቃቂ እየነከሱ ከማኅፀን አልወጡም። ሕዝብ የሚገዛው እንዲህ ነው ተብለው ጊንጥ የሚመስል አለንጋ የሰጣቸው አንዳች ኅይል የለም። ለምን ገዥና ተገዥ፣ ገራፊና ተገራፊ ሆነን ቀረን? አንመራመር። አስፈላጊ ወዳልሆነ እሽኰለሌም አንግባ። ይልቁን ከሞት በፊት ስላለው እኩልነት እናንሳ። በሞት ሕይወትን ስለማምጣት፣ በደምና በአጥንት ነፃነትንና እኩልነትን ስለመቀዳጀት።- ውይይይይ ለአፍ አይገድም። ትግሉን፣ መስዋዕትነቱን በወረቀት ላይ ጨረስነው አይደል? በሃያኛው ክፍለ ዘመን መነሻ የተጫነው የእኩልነት ትግል እነ W.E.B Du Bois የጀመሩት የጥቁር አሜሪካውያን ተጋድሎ ስትራተጂ የሚነደፍበትና ፕሮግራሙ በሥራ ላይ የሚውልበት ስልት የሚወጣበት ነበር። ታላቁ ዱብዋ ተፈጥሮ ለሰው ልጆች እኩል የሰጠችውን መብት ከሰው ልጆች መለመንን የመሰለ ውርደት እንደሌለ ይገልጣል። የመብትና የነፃነት ልመናን የመሰለ ወራዳ አቋም የለም። W.E.B Du Bois The Souls of Black Folk በሚል ድሮ ባሳተመው መጽሐፍ “ተነሥ! የምታጣው ሰንሰለትህን ነው” ወደሚለው የተራማጆች ፍልስፍና ያመራል። እንዲያውም ሎወልን በመጥቀስ-

Twixt old systems and the word
Truth forever on the scaffold
Wrong forever on the throne
yet that scaffold sways the future
And behind the dim Unknown
Standeth God within the shadow Keeping watch above His own

ይላል። እውነት ዘወትር በመሰቀያው ሥፍራ፣ ውሸትና የማይገባው ሁሉ ዘወትር በዙፋኑ (በአልጋው) ላይ የመገኘቱ ነገር- ያ የመሰቀያው ጣውላ የወደፊቱን ሁሉ እየነቀነቀ መገኘቱ፣ እነሆ በጭላንጭሉ መሐል ደግሞ እግዚአብሔር ከፍ ብሎ ቆሞ የራሱን ወገኖች የማበረታታቱ ጉዳይ ዘላለማዊ ነው።

ልመለስ ወደ አሜሪካ ዓመታዊ የሰብአዊ መብት መግለጫ። ከላይ ያነሳሁአቸው የዱብዋ (አሜሪካኖች ዱባይስ ይላሉ ፈረንሳዮችን ለማብሸቅ) ወይም የፍሬደሪክ ዳግላስ ታሪኮች ለእነሱ ብዙ ይጥማቸው እንደሆነ አላውቅም። በተለይ ለሪፐብሊካኖቹ። እንደዚያም ሆኖ ይህ በእነሱ ድጋፍና ርዳታ ሞልቃቃ ሆኖ የተወለደውና የሚጨፍርብን ሥርዓት (መንግሥት) ፀረ ሕዝብ፤ ፀረ አገር፣ ፀረ እንጨት፣ ፀረ ሳር፣ ፀረ ሕዝብ፣ ለመሆኑ- እደግመዋለሁ- የእነሱ እማኝነት አለን። ጊዜው- የመለያያው- ደረሰና ነው ምሥጢሩን ሁሉ ያፈነዱት? ሊሆንም ላይሆንም ይችላል። እዚያ ላይ ያለውን ነጥብ የምንመለስበት ይመስለኛል። ለአሁኑ ግን አሜሪካ በአንድ በኩል ልትረዳን የምትችላቸውን ጉዳዮች ባነሳ- ከአንባብያን ድጋፍ ካገኘሁ።

አንደኛ- እስካሁን ድረስ አሜሪካ እንዲህ ያለ በሰብአዊ መብት አከባበር ረገድ የተበላሸ አቋም፣ በፖለቲካና በአገር አንድነት ጥበቃው ረገድ አሳፋሪ ሪኮርድ፣ በሕዝብ ሰላም ጥበቃና የፍትሕ መስተንግዶ መላሸቅ ረገድ ያልሆነላቸውን መንግሥታት ወይ Evil ኤምፓየር- ወይ Rogue State አለዚያም አሸባሪ (Terrorist) ሲሉ ባጅተዋል። ወያኔ ምንድነው? በእኛ ምደባ Terrorist Regime ሊባል ይገባዋልና ስያሜው በዚሁ እንዲሆን እንጠይቃለን።

ሁለተኛ፥ ይኸ ሁሉ ከተወሳና የወያኔዎች መንግሥትም ከሕዝብ የብድርና የርጥባን ገንዘብ 20 ቢሊዮንዶላርስ ጠልፎ ወደግል ሂሳብ ያዋለ እንደመሆኑ- የዋና ዋና ሌቦችን የስም ዝርዝር እናቅርብና ወደየምዕራቡ መዲና ሲገቡ እንዲያዙና እንድንፋረዳቸው።- ገንዘባቸው እንዳይንቀሳቀስ እንዲደረግ- ከምዕራባውያን የሚሰጣቸው ማናቸውም ርዳታ ያለ ቅድመ ሁኔታ እንዲቋረጥ- ኢኮኖሚው ራሱ የተጠለፈና ወደ ግል ኩባንያነት የተዛወረ ስለሆነ የትኛውም አገር ከወያኔዎች ጋር የንግድ ልውውጥ እንዳያደርግ ዘመቻችንን እንዲቀበለን ትብብር እንጠይቃለን።- ከናይን ኢለቨን ጋር በተያያዘ አሜሪካ እንዳይደርሱ እግድ የነበረባቸው አንዳንድ ዘራፊና አቀባባይ ሌቦች እንደገና ወደ አሜሪካ ብቅ እያሉ የለመዱትን የሞራል ድቀት ትርኢታቸውን እያሳዩ ናቸው። ከእነዚህ መካከል አንዱን አረብ ግለሰብ የኢትዮጵያ ትውልድ ሁሉ የሚፋረደው ስለሆነ ተይዞ እንዲመረመር እንጠይቃለን። ወርቃችን፣ ሌሎች የማዕድን ሀብቶቻችን ወዘተ በዚሁ ሰው እንደ ትንሽ ዕቃ በየቀኑ እየተጫነ እንደሚወሰድ እናውቃለን። እናስረዳለንም። …………

በ1980ዎቹ Republic of Fear በሚል ርእስ ስለ ሳዳም ሑሴን ጨለማ አገዛዝ የሚያወሳው መጽሐፍ በእጅጉ ያሸማቅቃል። ጸሐፊው ኬናን ሜኪያ ይባላል። የኢትዮጵያ የዛሬ ሁኔታ ደግሞ ሌላ ባሕርይ ያለበት ይመስለኛል። ስለ ዋናዎቹ አምባገነኖች ሲነሣ አብዛኛዎቹ ነጠላ ናቸው። በቺሊ ፒኖቼ- በሩማንያ ቻይቼስኮ፣ በኢራቅ ሳዳም ሑሴን፣ በሊቢያ ጋዳፊ…ናቸው። ለወርቅ ጥጃቸው የማይንበረከክ፣ ለምስላቸው የማይሰግድ ከሁለት ስፍራ ይከፈላል። ያማቸው፣ ስማቸውን ያጐደፈ…የሚሰቃይበት አዳዲስ መሣሪያ አስፈልፍለዋል። ዝርዝር የማሰቃያውን ስልትና ድርጅት ከማእከላዊ ምርመራ ሠራተኛነት አምልጠው የወጡ ሰዎችን ማነጋገር ይቻላል። ባይሆን አንድ ጥያቄ በአእምሮአችሁ የሚመላለስ ወገኖቼ አትታጡም። መለስ ከሞተ በኋላም ይኸ አገር በአምባገነን የሚመራ ነው ለማለት ይቻላል ወይ? በእኔ በኩል ከሰዎች ጋር ስወያይ “አምባገነኑ የማይታወቅ አምባገነን መንግሥት” A Dictatorship without a Dictator ግን አገዛዙ መንጋ ጨካኖች፣ ነፍሰ- ገዳዮችና በዝባዦች ቢኖሩትስ? የፈረንሳዩ ታላቅ ምሁር ዣን ፍራንስዋ ሬቨል Without Marx or Jesus በሚለው መጽሐፉ እንዲህ ያሉትን አምባገነኖች ባሕርይ Collective Mediocrity and Collective bestiality ይለዋል። ነገሩ እንዲህ ነው። መለስ ሲሞት የእሱ እጓለማውታ (Orphans) መፈላለግ ያዙ። ሰብሳቢ አጣን ብለው ወደ ትካዜው ዓለም ተሰደዱና መጠራራቱን አንድ መፍትሔ አደረጉት። ምንጣፉን ቶሎ ብለው የረገጡት እነ እንቶኔ ደግሞ አራት ኪሎን የተጫጫነውና አሁንም የሚገዛውን መንፈስ በፍጥነት በማናቸውም አስማት ለማስወጣት አልቻሉም። ትንሽ ፋታ ሳያስፈልጋቸው አልቀረም። ጥቂት ጊዜ ከገዙ በኋላ የፕሮፓጋንዳውም መሣሪያ ትንሽ ትንሽ ይደፍረዋል። “መለስኮ ሰው ነው” ማለት ይጀምራል። ሰው መሆኑን ዛሬ ነው ያወቁት አትበሉአቸው። እኛ መለስን ከመቃብር አውጥተን አንፋረደውም። እነሱ ራሳቸው ከሳሽም ፈራጅም ይሆናሉ። ጠብቁ ብቻ።

በደርግ ጊዜ ስለአባካኝነትና አሻጥር ትልቅ ጉባኤ ተዘርግቶ ነበር። በንቁዝ (ኮራፕት) ባለሥልጣኖችና በመሳሰሉት ላይ ጥብቅና ወሳኝ የሆነ ርምጃ ስለሚወሰድበት ሁኔታ ውይይት ሲካሄድ በየቦታው ኮሚቴዎች እንዲቋቋሙ አሳብ ይቀርባል። በዚያ መድረክ ላይ የአገር አስተዳደር ሚኒስትር የነበሩት ጄኔራል ታዬ ጥላሁን የተናገሩት ትዝ ይለኛል። በአጤ ምኒልክ ዘመን እቴጌ ጣይቱ “ለአገሬ ለየጁ ያለው አንድ አፈንጉሥ ብቻ ስለሆነ ሌላ እንዲጨመርለት እጠይቃለሁ” ሲሉ እቴጌይቱን በአደባባይ ተቃውመው የማያውቁት ንጉሠ ነገሥት “እንኳን ሌላ ተጨምሮበት አንዱም ቢሆን አልተቻለም” አሉ ይባላል።

በዛሬዪቱ ኢትዮጵያ ከመለስ ሞት በኋላ አንድ ታዋቂና በአደባባይ ስሙና ሹመቱ የተገለጠ አምባገነን ባይኖርም ሟቹ በመጠኑ ራቅ ያደረጋቸው ሰዎች አልጋው ላይ የተረባረቡ ይመስለኛል። አቦይ ስብሐት፣ ጌታቸው አሰፋ፣ ዐባይ ወልዱ፣ ደብረጽዮን ገብረሚካኤል ወዘተ ወዘተ…በአንድ አገር የስለላው መረብ እንዳለ ወደ ፍጹማዊ ኅይል ሲለወጥ ደግሞ የዜጐች ሁሉ (መካከለኛ ደረጃ ያሉት ወያኔዎች ሳይቀሩ) መብት ወደ ኢምንትነት ይለወጣል። የሥነ መንግሥት ምሁራን በመንግሥት ውስጥ መንግሥት (ኤስቴት ዊዝን ኤ ስቴት) የሆነውን እንዲህ ያለውን ሥርዓት “መሪ” የሚባለውን ግለሰብ ጭምር ሽባ አድርጐ የሚቀፈድደው ያደርጉታል። በአሁኑ ሁኔታ ቀስ በቀስ የመለስ የቅርብ ሕዝብ አጫራሾች ዕጓለማውታ (ኦርፋንስ) ቢመስሉም ሌሎች በርካታ አምባገነኖች ጡንቻቸውን እያፈረጠሙ ናቸው። ወትሮ አንድ አምባገነን ያልቻለው የኢትዮጵያ ሕዝብ የብዙ አምባገነኖች ተሸካሚ ሆኖዋል። ሁሉም ነፍሰ ገዳዮች! ነፍሰ ገዳይ የማይፈራስ ማነው?

ለጊዜው በመንጋ ተንኮለኞች- ነፍሰ ገዳዮችና የዝርፊያ ሠራዊት እየተገዛን እንገኛለን። ስለእነሱ ድግስ፣ ስለ እነሱ ጥቅም፣ እነሱ የትኛዋን ጋለሞታ እንደሚጐበኙ፣ የትኛዋን መለኮን ዛሬ እንደወሰዱ እንወያያለን። በጥቃቅን ጉዳዮች አእምሮአችንን አስጨንቀናል። ወጣጥረነዋል። ይልቁን በሌላው ዓለም እየተቀጠቀጠ ማረፊያ ያጣው መንግሥታዊ አሸባሪነት የሙጥኝ ብሎ የሚገኘው በኢትዮጵያ መሆኑን እንተባበር። ይህን የሽብር መንግሥት ሌላው ቀርቶ በብረት መሞከርን ካህናቱና መነኮሳቱም መደገፍ አለባቸው። ከቶውንም ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ በፋሺስቶች ጥይት ሊደበደቡ ጥቂት ሰከንዶች ሲቀራቸው “ልጆቼ ኢትዮጵያውያን ለፋሺስቶች እንዳትገዙ አውግዤአለሁ” ማለታቸው ይጠቀሳል። አዳዲስ ካሕናትና የዚህ ትውልድ ቀሳውስት ነገሩን ቸል እንኳ ቢሉ የአቡነ ጴጥሮስ ግዝትና ውግዘት አለብን። ቋሚ ነው- እስከማዕዜኑ።

ትግልና ታጋይ የሚጠይቁት አንድ ነገር ብቻ ነው። በደረትህ ውስጥ ጤነኛ ልብ፣ በጭንቅላትህ ውስጥ ጤናማ አእምሮ ካለህ ማናቸውም ችግር አይፈታህም። ጥይት አይመታህም። ድንፋታ ትርጉም አይሰጥህም። ቅጥፈትና ማስፈራራት ትጥቅህን አያስፈታህም። ልጆቼ ልላቸው የምችለው እነ እስክንድር፣ በቀለ፣ አንዱአለምና ርእዮት ይህን ወኔ በሰፊው የተቀዳጁ ናቸውና እንኮራባቸዋለን። እነሱ ወኅኒ ዓለም ሲገቡ የከዳናቸውና የቆሙለትን ዓላማ ጭምር የረሳንባቸው ከመሰላቸው ደግሞ አደራ በላነት ሊሰማን ይገባል።

ይህን ጽሑፍ የጀመርሁት በወያኔ የልደት በዓል ምክንያት ትንሽ የምለውን ለማቃመስ ነበር። ምናልባትም እንደ ፍሬደሪክ ዳግላስ ለእነዚህ ሰዎች “ጉንበት 20- ጉንበት ሃያ ትሉናላችሁ ጉንበት ሃያ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የሥቃይ ሁሉ እናት የሆነችው ስቃይ የመጣችበት ቀን። ጉንበት 20 የባርነትና ወደር የሌለው ውርደት መታሰቢያ ቀናችን ናት። ጉንበት 20 ለእሥራታችን መታሰቢያችን ናት።” ልንላቸው እንችላለን። ይኸ የደፋሮቹ ጋዜጠኞች – የጀግኖቹ የፖለቲካ መሪዎችና ገበሬዎች የተባበረ ድምጽ ነው። በሬሳችን ላይ የሚጨፍሩበት፣ በመቃብራችን ላይ የሚያሽካኩበት፣ ቤትና ንብረት አሳጥተው ለስደት ያበቁንና በዚህ ደስታ የሚሰክሩበት በዓላቸው- የእኛ የልቅሶ ዕለት፣ የእኛ የመከራ ቀን መታሰቢያ ነው።

በመጨረሻም እንደገና ለአሜሪካ በማቀርበው ጥያቄ ላይ ይህችን ነጥብ እደግማለሁ። ይህ መንግስት ኢቭል የምትሉት አይነት ነው? ወይስ አሸባሪ? የወያኔ ኦሮሞዎች በኢትዮጵያውያን ኦሮሞዎች ላይ የሚፈጽሙትን እልቂት፣ የወያኔ አማራዎች (እነበረከት አምሮች ከተባሉ) በኢትዮጵያውያን አማሮች ላይ የሚያካሄዱትን መጠነ ሰፊ ድምሰሳ፣ የወያኔ ሙስሊሞች በኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ላይ እያደረሱ የሚገኙትን ወከባና ወደር የሌለው ጥቃት፣ ሟቹ የመለስ የሃይማኖት የይስሙላ ፓትርያርክና እንደ ሩሲያዊው ራስፑቲን የሚቆጠረው አባ ጳውሎስ በኢትዮጵያ አብያተ ክርስቲያናት ላይ ያካሄደውን ሥቃይ አሜሪካ ከእኛ በላይ እንደማያውቀው ለዴሞክራሲ፣ ለሰብአዊ መብትና ነፃነት ስትል ርምጃ ለመውሰድ አቅዳለች? አጤ ኅይለሥላሴ በቀድሞው የመንግሥታት ማኅበር ጉባኤ ላይ ያደረጉትን ንግግር ለመጥቀስ እገደዳለሁ – “ታሪክና ትውልድ ፍርዳችሁን ይጠባበቃሉ!”
እነሆ ዛሬ በኢትዮጵያ የሰው ዘር ጠላት የሆነ ሥርዓት አለ። የሒትለርን ፀረ ሕዝብነት ለመረዳት የፖላንድ መወረር፣ የሃምሳ ሚሊዮን ሕዝብ ማለቅ፣ የስድስት ሚሊዮን አይሁድ መጨፍጨፍ መጠበቅ ይገባል? ታሪክ አላስተማራችሁምን? በአሜሪካ ላይ ስንት ክህደትና ቸልታ እንቁጠር? በፋሺስት ወረራ ዘመን ሩዝቬልትና ሴክሬተሪ ሐል ያሳዩን ክሕደትና ቸልታ አይረሳንም። አሜሪካ የበለጠ ትናገር! እግዚአብሔር ሁላችሁንም ይጠብቃችሁ!!

http://ecadforum.com/

posted by Tseday Getachew

ከባዶ ጭንቅላት ባዶ እግር ይሻላል! (ግንቦት7)

Ginbot 7 weekly editorialየባህርዳር እና አካባቢው ሕዝብ ከባዶ ጭንቅላት ባዶ እግር ሺህ ጊዜ እንደሚሻል አካሉን ብቻ ሳይሆን ህሊናውንም ለትግራዩ ነፃ አውጪ ህወሓት ባርነት ላስገዛው “የብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን)” እያለ እራሱን ለሚጠራው ድርጅት መሪዎች ተናገረ።

ባርነት ክፉ ነው። በባርነት ላይ የጭንቅላት ባዶነት ሲታከልበት ደግሞ አለምነው መኮንንን የመሰሉ የብአዴን መሪዎችን ይፈጥራል። የብአዴን መሪዎች ለጌታቸው ህወሓት ያላቸውን ታማኝነት ለማሳየት ራሳቸውን ማዋረዳቸው ሳያንስ እንወክለዋለን የሚሉትን ሕዝብ በጅምላ መስደባቸው ብአዴን እንደ ድርጅት የሚገኝበት የተዋረደ ደረጃ ያሳያል።

ህሊና ያለው ባርያ ዛሬ ነፃ ባይሆንም ወደፊት ነፃ የመውጣት ህልም አለው። ዛሬ በጉልበተኛ የባርያ አሳዳሪ ነፃነቱን ቢያጣም የህሊና ነፃነቱን ያላስደፈረ ባርያ ለነፃነት መታገሉ የማይቀር ነው። እንደ ብአዴን መሪዎች በታማኝ ባርያነቱ እየፈነጠዘ ያለ ባርያ ግን ነፃ ሰው የመሆን ህልሙንም ጭምር አጥቷል። እንዲህ ዓይነቱ ባርያ በአካልም፤ በመንፈስም ባሪያ ነው። ነፃ ሰው የመሆን እድል የለውም።

የአማራ ሕዝብ ብአዴንን የመሰለ አሳፋሪ ድርጅት በታሪኩ ገጥሞት አያውቅም። በፋሽስት ጣልያን ወረራ ጊዜ ለጠላት ያደሩ ባንዶች እንኳን ከዛሬዎቹ ብአዴኖች የተሻለ ክብር ነበራቸው። እነሱም ከዛሬዎቹም በተሻለ በጌቶቻቸው ጣሊያኖች ይሰሙ ነበር። በገዢዎቹ ለመወደድ የራሱን ሕዝብ የሚዘልፍ፣ የሚሰድብና የሚያዋርድ እንደ ብአዴን ያለ አዋራጅ ድርጅት በአማራ ምድር አልታየም።

ለዚህም ነው የባህርዳር እና አካባቢው ሕዝብ የብአዴንና የወያኔን አፈናዎችን በጣጥሶ የካቲት 16 ቀን 2006 ዓ.ም. ቁጣውን በባዶ እግሩ አደባባይ በመውጣት የገለፀው። እግር ባዶ መሆኑ ጭንቅላት ባዶ የመሆኑ ያህል የሚያሳፍር አይደለም። ድህነት ወንጀል አይደለም። ነፃ አዕምሮና የሕዝብ ይሁንታ ያገኘ አስተዳደር ካለ ድህነትን ማሸነፍ ይቻላል።

ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ ፈታኝ ሁኔታዎችን ተቋቁመው የየካቲት 16 ቀን 2006 ዓ.ምን ሕዝባዊ ተቃውሞ ላደራጁና በተቃውሞውም ለተካፈሉ ሁሉ ያለውን አክብሮት ይገልፃል። ሕዝብ ብሶቱን የሚገልጽበት ሕዝባዊ ተቃውሞ ማደራጀትና መምራት መቻል ትልቅ ነገር ነው። ሕዝባዊ ተቃውሞዎች ወደ ሕዝባዊ እምቢተኝነት የማደግ እድል አላቸው። ስለሆነም ግንቦት 7 ለባህርዳሩ ሕዝባዊ ተቃውሞ አደራጆችና ተሳታፉዎች “እንኳን ደስ ያላችሁ” በማለት የትግል አጋርነቱን መግለጽ ይሻል።

ግንቦት 7፣ ብአዴንን ከአባላቱ ለይቶ ማየት ይሻል። ከዚህም በተጨማሪ የብአዴንን ከፍተኛ አመራር ከሌላው ለይቶ ይመለከታል። ብአዴን ነፍሳቸውን ሳይቀር ለወያኔ በሸጡ ሰዎች የሚመራ፤ ነፃ የመውጣት ተስፋ የሌለው ራሱ ባርያ የሆነ ድርጅት ነው። አባላቱ ግን ከዚህ የተለዩ ሊሆኑ እንደሚችሉ ግንቦት 7 ያውቃል።

ግንቦት 7፡ የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ከዚህም በፊትም ደጋግሞ እንደገለጸው፤ በተለያዩ ጊዜያት ራሳቸውን ከወያኔ ባርነት ነፃ ለማውጣት በወሰዱት እርምጃ መስዋእትነት የከፈሉ የብአዴን አባላት መኖራቸውን ያውቃል። ግንቦት 7 ለእነዚህ ቆራጦች ትልቅ አክብሮት አለው። ዛሬም ህሊናቸውን ሙሉ በሙሉ ያልሸጡ የብአዴን አባላት አሉ ብሎ ያምናል። እነዚህ ወገኖቻችን ራሳቸውን ነፃ ለማውጣት የግል፣ የወገንና የአገር ግዴታ አለባቸው ብሎ ያምናል።

ስለሆነም ዛሬም ይህንን አጋጣሚ ተጠቅመን ጥሪዓችንን እናድሳለን።

የብአዴን አባላት ሆይ!!! የገዛ ራሳችሁን፣ የአማራን ሕዝብ እና ኢትዮጵያን እያዋረደ ካለው ብአዴን ተላቀቁ፤ አሊያም እውስጡ ሆናችሁ ድርጅቱን ግደሉት። የብአዴን መኖር ለወያኔ ካልሆነ በስተቀር ለማንም አይበጅም። ነፃነት ካለ ድህነትን በሥራ ማሸነፍ ይቻላል። ሰው ባርያ ሆኖ በሀብት ቢንበሸበሽ ምን ይፈይድለታል?

የብአዴን አባላት ሆይ!!! ወደ ህሊችሁ ተመለሱ። ራሳችሁንም የበደላችሁትን ሕዝብ የመካስ እድል አድል አላችሁ ተጠቀሙበት። ይህንን ባታደርጉ ግን ለገዛ ራሳችሁ ፀፀት፤ ለልጆቻችሁ ሀፍረትን የምታወርሱ መሆኑን አትዘንጉ። ወያኔ መሸነፉ በጭራሽ የማይቀር መሆኑን እያወቃቸው በድህረ ጣልያን ወረራ ባንዶች ያገኙትን ምህረት እናገኛለን ብላችሁ አታስቡ።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!

posted by Tseday Getachew

በንፋስ ስልክ ላፍቶ የመንግስት ታጣቂው የባለ3 ልጆች ባለትዳሮችን በጥይት ደብድቦ ገደለ

ምኒልክ ሳልሳዊ እንደዘገበው 

በንፋስ ስልክ ላፍቶ የመንግስት ታጣቂው የ3 ልጆችን ባልና ሚስትን በጥይት ደብድቦ መግደሉ ተሰማ። ድርጊቱ የተፈፀመው ትላንት ከቀኑ 9.30 አካባቢ ነው ተብሏል።

አዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ውስጥ ልዩ ስሙ መካኒሳ አቦ ማዞሪያ በሚባል አካባቢ አንድ የመንግስት ታጣቂ የሶስት ልጆች ወላጆች የሆኑትን ባልና ሚስት በአውቶማቲክ መቺንገን በጥይት ደብድቦ ገድሏቸዋል።

የአካባቢው ሰዎች እና የሟች ዘመዶች በጋራ በመሆን የቀብሩን ስነ- ሥርዓት ለማስፈጸምና የመንግስት ታጣቂው የወሰደው እርምጃ ለማውገዝ እና በየጊዘው በአካባቢው የሚፈጸመውን የመንግስት ታጣቂዎች እርምጃ እና በህብረተሰቡ ላይ የደረሰውን ግፍ በጋራ ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር ለማጋለጥ በህብረት ድምጻቸውን ለማሰማት ሲሞክሩ በፈደራል ፖሊስ የተበተኑ ሲሆን በአካባቢው ላይ የአዲስ አበባ የፖሊስ ሃይሎች ተሰማርተዋል።

የፈደራል ፖሊስ አመራሮች የአከባቢውን ህዝብ የፖለቲካ አጀንዳ ያለው ሲሉት የፈረጁት ሲሆን ቀብሩ ሳይፈጸም ህዝቡን በማስፈራራት እና በዛቻ ያባረሩት ሲሆን የሟች ዘመዶች የኢትዮጵያ ህዝብ ይህን ጉዳችንን ሳይሰማና ሳያውቅልን አንቀብርም ብለው አስከረኖቹ ወደ መኖሪያ ቤት ተመስልሷል።

ለዘ-ሐበሻ ዘግየት ብሎ በደረሰን መረጃ ቀብሩ በነገው እለት ይፈጸማል።

Ze-Habesha

posted by Tseday Getachew

Post Navigation